Saturday, July 14, 2012

በበርካታ መጽሐፍቶቹ የሚታወቀው የዲያቆን አሸናፊ መኮንን ጉዳይ አነጋጋሪነቱ እንደቀጠለ ነው።


 D/n Ashenafi case: Click here to read in PDF
ዺ/ን አሸናፊ በሲኖዶሱ ስብሰባ ወቅት ግንቦት 9 ያስገባው ደብዳቤ
የሰኔ 25 የዲያቆን አሸናፊ አቤቱታ
(ሐምሌ 7 2004 ዓ.ም. ፣አውደ ምህረት/www.awdemihret.blogspot.com) “…የምንሠራው ሥራ ከሌላ ሥራ ሊኖር እንደማይችል ሁሉ የምንኖርለት ዓላማ ከሌለም ትክክለኛ ሕልውና ሊኖር አይችልም፡፡ በርግጥ ሰዎች የሚኖሩለት ነገር ሁሉ ዓላማ ተብሎ ሊጠራ አይችልም፡፡ ዋነኛ ዓላማው እግዚአብሔርን ማወቅና መከተል ነው፡፡ ሌሎች ዓላማዎች ሁሉ ከትልቁ ዓላማ ውስጥ የሚወጡ ናቸው፡፡
አንድ ሰው የሰው ዋጋው ስንት ነው? ብሎ ከጠየቀ በኋላ የሰውን ዋጋ ለማወቅ እግዚአብሔርን ጠይቁት ብሏል፡፡ አንድ ዕቃ የራሱን ዓላማና ዋጋ ማስረዳት አይችልም፡፡ የዕቃው ዝርዝር ዓላማና ዋጋ ያለው ራሱ ጋ ሳይሆን ሠሪው ጋ ነው፡፡ ስለዚህ የዕቃውን ዓላማና ዋጋ ለማወቅ ሠሪውን መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡ አዎ የሰው ልጅ ለትልቅ ዓላማ የተፈጠረ ፍጡር ነው፡፡ ይህንንም ሊያሳውቀን የሚችል እግዚአብሔር ብቻ ነው፡፡
 ሕይወት ግባችንን ትጠይቀናለች፡፡ መድረሻችንን ካላወቀች በነጻነት አትለቀንም፡፡ እግዚአብሔር በዓላማ ፈጥሮናል፡፡ በአጋጣሚ ወይም በስህተት አልተፈጠርንም፡፡ የተፈጠርንበት ዓላማም እኛ ዓላማ ከምንለው ከመውለድ መክበድ ያለፈ ነገር ነው፡፡ የክርስትናው ጉልህ ነጥብ እግዚአብሔርን መቀበልና ራስን መቀበል ነው፡፡ ብዙዎች ራሳቸውን ሳይቀበሉ እግዚአብሔርን ተቀብለናል ይላሉ፡፡ ከዚህ ነገር የተነሳም በክርስትናቸው ደስታ የላቸውም፡፡ ባለዓላማ የሚያደርገን እግዚአብሔርንና ራሳችንን መቀበል ነው፡፡
እግዚአብሔርን ስንቀበል የምናገኘው የመጀመሪያው ጸጋ ራሳችንን መቀበል ነው፡፡ ቀለማችንን፣ ዘራችንን፣ ቋንቋችንን፣ ቤተሰባችንን፣ ማንነታችንን እንቀበለዋለን፡፡ እግዚአብሔር የሰጠን ማንነት መለወጥ የማንችለው መለኮታዊ ምርጫ ነው፡፡ በዓለም ላይ እኛን የምንመስል እኛ ብቻ ነን፡፡ እግዚአብሔር ግልባጭ የሌለን ኦርጂናል አድርጎ ፈጥሮናል፡፡ በመልካችን፣ በአመለካከታችን፣ በተሰጦአችን፣ በትከሻችን፣ በአረማመዳችን፣ በድምፃችን፣ በአሻራችን፣... ልዩ ነን፡፡ ፊትን በምታህል ትንሽ ገጽ  ስድስት ቢሊየን ሕዝብ የተለያየ መልክ ተስሎበታል፡፡ ይህ የሰው ሥራ ቢሆን አንዱ ሰው ስንት ጊዜ በተደገመ ነበር፡፡ 

ስለ ጠባያችን እንጂ ስለዘራችን፣ ስለ ምርጫችን እንጂ ስለ አፍንጫችን አንጠየቅም፡፡ ስለዚህ በሆንነው ነገር ደስ ሊለን ይገባል፡፡ ሌሎችን ላንሆን ራሳችንን ማጣጣል አይገባም፡፡ እኛ ራሳችንን ስንሆን ሌሎችም ራሳቸውን ሲሆኑ እግዚአብሔር ከላይ ወደ ታች ሊያየው የፈለገው ኪነ ጥበብ ይሟላል፡፡ ማይክል ጃክሰን የጥቁር ቆንጆ ነበር፡፡ ራሱን ግን መቀበል ስላልቻለ ዛሬ የመፍረስ አደጋ ተጋርጦበታል፡፡ ራስን አለመቀበል ፈረንጅም ያልመለሰው ጥያቄ ነው፡፡ ብዙዎች ራሳቸውን ከፎቅ ላይ የሚወረውሩት ራሳቸውን መቀበል እያቃታቸውና የሚኖሩበትን ዓላማ በውል መግለጥ አለመቻላቸው ነው፡፡ በምዕራቡ ዓለም እኔ ሂትለር ነኝ እያሉ እንደ ሂትለር የሚለብሱና የሚናገሩ አሉ፡፡ ራስን አለመቀበል ዓላማ የለሽ ያደርጋል፡፡ አልሞ ተኳሾችን በአሜሪካ የወለደው ራስን አለመቀበል ነው፡፡ ጃማይካዎች የሞቱትን  ኃይለ ሥላሴን እንዲያመልኩ ያደረጋቸው ይኸው የማንነት ቀውስ ነው፡፡ ሀሺሽ የሚያጨሱ የትምህርት ችግር ያለባቸው አይደሉም፡፡ እንደውም ብዙዎቹ የተማሩ ናቸው፡፡ የማንነት ጥያቄ ነው፡፡ የማንነትን ጥያቄ የሚመልሰው እግዚአብሔር ብቻ ነው፡፡ ዓላማዬ ምንድነው? በማለት ዓላማን ማግኘት አይቻልም፡፡ እግዚአብሔር በእኔ ላይ ያለው ዓላማ ምንድነው? ስንል ትልቁን ዓላማችንን ያኔ እናገኘዋለን፡፡…”
ይህን ጽሁፍ የምናገኘው ከዲያቆን አሸናፊ መኮንን ራዕይ ያለው ትውልድ  መጽሐፍ ውስጥ ነው። ይህን መጽሐፍ የጻፈው ዲያቆን ዛሬ ሳይጠየቅ ሳይመረመር ምላሸ ሳይጠየቅ የተከሰሰስኩት በምንድን ነው አስታውቁኝ ብሎ  እየጠየቀ ፊታችን አትቆምም ተብሎ ተወግዟል። እነዚህ መጽሐፍት ለትውልዱ መጽናናት የሆኑ ለበርካታ የትውልዱ ጥያቄዎች ምላሽ የሰጡ መጽሐፍት ናቸው።
ከ16 በላይ መንፈሳዊ መጽሐፍት ደራሲ የሆነው ዲ/ን አሸናፊ መኮንን ሥራቸው ገኖ ታሪካቸው በአነስተኛ ደረጃ ከሚታወቁ የቤተ ክርስቲያን ልጆች አንዱ  ነው። በ13 ዓመቱ የመድረክ አገልግሎት ከጀመረበት ጊዜ አንስቶም ህጻኑ ሰባኪ እየተባለ በየቤተክርሰቲያን መድረክ ላይ ሲቆም እንደነበር የሚታወስ ነው። በመንፈሳዊ ሕይወቱ እጅግ የተመሰገነ ማንነት አለው የሚባለው ዲያቆኑ በከፍተኛ ህመም የመድረክ አገልግሎት ካቆመበት ከ1989 ዓመተ ምሕረት ጀምሮ የጽሑፍ ሥራ ላይ አትኩሮ የተለያዩ ሥራዎችን ሠርቷል፡፡ የተለያዩ መንፈሳዊ ጽሑፎችን ከ1986 ጀምሮ ይጽፍ የነበረው ዲያቆኑ የመጀመሪያውን መጽሐፉን በ1995 ያሳተመ ሲሆን ከዚያን ጊዜ ጀምሮ 16 መጻሕፍትን አሳትሟል፡፡ መጻሕፍቱ በቤተ ክርስቲያን ምእመናን ዘንድ ከፍተኛ ተቀባይነት ያላቸው ሲሆኑ በቤተ ክርስቲያናችን ያለውን የክርስትና ሕይወትን የሚመለከት መጻሕፍት ክፍተት ያሟላ ሰው ነው። ቤተ ክርስቲያናችን የዶግማና የቀኖና መጻሕፍት በብዛት እንዳሉዋት ቢታወቅም የብዙዎቻችን ችግር የሆነውን ስለ ሃይማኖታችን ካወቅን በኋላ ክርስትናን እንዴት እንኑር? የሚለውን ጥያቄ የሚመልሱ መጻሕፍት በብዛት መውጣት የጀመሩት ግን  ዲያቆኑ የእግዚአብሔር ትዕግሥት የሚለውን መጽሐፍ ካሳተመ በኋላ ነው።
የአጻጻፍ ዘዴው እጅግ መሳጭ የሆነ፣ የታሪክ አወራረዱ የሚያስደንቅ የጭብጥ አገላለጽ መንገዱ እጅግ የሚያረካ የሆነው እና  የሕይወት ልምድን እና በርካታ ምሳሌዎችን የያዙት መጻሕፍቱ በርግጥም ሰዎችን የመለወጥ አቅም ስላላቸው በርካታ ሰዎች በመጽሐፉ እንዲሳቡና ሕይወታቸው እንዲለወጥ ምክንያት የሆነ ወጣት ጸሐፊ ነው። አስካሁን ድረስ ወደ 250,000 የሚጠጉ የተለያዩ መጻሕፍቱን  ኮፒዎችን ያሳተመው ዲያቆኑ ባለፉት 10 ዓመታት ውስጥ በሀገራችን በርካታ መጻሕፍትን በመጻፍና በርካታ ኮፒዎችን በማሳተም ቀዳሚው ሰው ነው።
አሸናፊ ማነው? መልኩስ ምን ይመስላል? የሚለው ጥያቄ ብዙዎች ልብ ውስጥ የሚመላለስ እንደሆነ ሲታወቅ ማኅበረ ቅዱሳን በአንድ ወቅት የመጽሐፉ በከፍተኛ ደረጃ መሸጥ አሳስቦት አደረኩት ባለው “ጥናት” “አሸናፊ የሚባል ሰው የለም አሸናፊ መኮንን ማለት የብዕር ስም ነው። በምንም መንገድ ቢሆን አንድ ሰው በዓመት ሁለትና ሦስት መጽሐፍ ሊያሳትም አይችልም። ስለዚህ አሸናፊ የብዕር ስም ነው” የሚል ድምዳሜ ላይ ደርሶ እንደነበር ይታወቃል። በርግጥም ከላይ ከተሰጠ ጸጋ ካልሆነ በቀር እንዲህ ዓይነት መጽሐፍ በዚህ ዓይነትና ምሥጢር፣ ጥራትና መልእክት ሊሠራ እንደማይችል የታመነ ነው። የማኅበርዋ ሰዎች ግን ለጸጋ እና ስለጸጋ ያላቸው ዕውቀት አነስተኛ ስለሆነ በሎጂክ ነገሩን ለመመዘን ተገድደዋል። ዲ/ን አሸናፊ ካሳተማቸው 16 መጽሐፍት በቁጥር የሚበልጡ መጻሕፍትን ጽፎ ያስቀመጠ መሆኑ ሲታወቅ አሁንም ሌሎች አዳዲስ መጻሕፍትን እየጻፈ እንደሆነ ተሰምቷል።
ማኅበረ ቅዱሳን የዲያቆኑ መጻሕፍት በከፍተኛ ደረጃ መሸጥ የእነሱን መጻሕፍት ገበያ  ስለጎዳው ካለፉት 5 ዓመታት ጀምሮ የዲያቆኑ መጻሕፍት እንዳይሸጡ ከፍተኛ እንቅስቃሴ እያደረጉ የነበረ ሲሆን የሚያደርጉዋቸው እንቅስቃሴዎች ሁሉ የመጽሐፉን ገበያ ማስቆም ስላልቻሉ ካልተወገዘልን አናርፍም በማለት ድንጋይ ነክሰው ከአምና ጀምሮ ተንቀሳቅሰዋል።
አምና የግንዛቤ ማስጨበጫ በማለት በየአዳራሹ ቅስቀሳ ባደረጉበት ወቅት ደረስንበት ያሉትን “መረጃ” ያቀረቡ ሲሆን ስለዲያቆኑ ያቀረቡት “መረጃ” ፍጹም ሐሰትና የመረጃ ክፍላቸው ምን ያህል ዘረክራካና ዲያቆን ዳንኤል እንዳለው ወሬ ለቃቃሚ መሆኑን ያሳየ ነበር። በዚህ ግንዛቤ ማስጨበጫ ላይ ከብሥራተ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን የተባረረ ነው ብለው በድፍረት የተናገሩ ሲሆን መጻሕፍቱን እንኳ አንብበው ቢሆን ያደገበት ቤተ ክርስቲያን ብሥራተ ገብርኤል ሳይሆን ሰበታ መካነ ሰላም ቅዱስ ገብርኤል ቤ/ክ እና ቤተ ደናግል ገዳም መሆኑን ይረዱ ነበር። እነ ወሬ እውቀቴ ግን ለስንት ዓመት አጥንተን ደረስንበት ያሉት “መረጃ” ከመሠረቱ በውሸት የተሞላ መሆኑ የመረጃ ክፍሉን አሠራር ተራነት ያሳየ ነው።
በልዩ ልዩ መንገድ መጽሐፉን ለማጥፋት ያደረጉት ሙከራ ስላልተሳካላቸው በመጀመሪያ ያደረጉት በየመዝሙር ቤቱ እየዞሩ የመናፍቅ መጽሐፍ ነው አትሽጡ የሚል ቅስቀሳ ቢሆንም አብዛኛዎቹ መዝሙር ቤቶች ግን መጽሐፉ ላይ ያለውን ስህተት አሳዩን እና መሸጥ እናቁም የሚል ጥያቄን በመጠየቃቸው እና ማሳየት የሚችሉትም ስህተት ስለሌለ የማስቆም ሙከራቸው ሳይሳካ ቀርቷል። በየክፍለ ሀገሩ ያሉትን የመጽሐፉ አከፋፋዮችን ግን መናፍቅ ናችሁ ብለን እናስወግዛችኌለን በማለት እያስፈራሩ እንዳይሸጡ ለማድረግ ያደረጉት ሙከራ መጽሐፉን ማስቆም ባይችሉም ከአደባባይ ሰወር አድርገው እንዲሸጡ አድርጎአቸዋል። በሕዝብ ፍላጎት እንጂ መጽሐፍ በነጋዴ ፍላጉት ብቻ እንደማይሸጥ ስላልገባቸው የአታንብቡ ሩጫቸው እንደ ማስታወቂያ ሥራ ተቆጥሮ ብዙ አንባቢዎችን ከማፍራት ያለፈ የፈየደው ነገር የለም፡፡
በዚህ የግንዛቤ ማስጨበጫ ፕሮግራሙ ሰበብ አታንብቡ በማለት ከዲያቆን አሸናፊ መጻሕፍት ለምሳሌነት የሚጠቅሱአቸው እነ የኑሮ መድኅን፣ ይቅርታ የእግዚአብሔር ትዕግሥት፣ ምክር ለወዳጅ የሚሉት መጻሕፍት እንዲያውም ከበፊቱ የበለጠ መሸጥ መጀመራቸው እና አታንብቡ እያለ የሚቀሰቅሰውን ማኅበር የዲያቆኑ የማስታወቂያ ሠራተኛ አስመስሎት እንደነበር ያነጋገርናቸው የመጻሕፍት ነጋዴዎች ገልጸውልናል።
አንዴ ከጀመሩት ተው ተው የማይሉት መጻሕፍቱ የብዙዎችን ጥያቄ ለመመለስ እግዚአብሔር የተጠቀመበት መንገድ መሆኑን በሚያረጋግጥ መልኩ የብዙዎች መንፈሳዊ ሕይወት የተፈወሰበት መሆኑ እርግጥ ነው። 
የማኅበረ ቅዱሳን “የመረጃ” ክፍል አባላት ዲ/ን አሸናፊ የብዕር ስም ሳይሆን በርግጥ በሕያውነት ያለ ሰው መሆኑን ሲያረጋግጡም በዓመት ውስጥ የሚጽፋቸው መጻሕፍት ብዛት የአንድ ሰው ውጤት ነው ለማለት ስላላስደፈራቸው የእርሱ ሥራ አይደለም ለማለት ሌላ መላ ምት ማፈላለግ ጀመሩ። እንዴት ያለ ጭንቅላት እንደደረሰበት ባናውቅም የተደረሰበት መላምት ግን አስቂኝም አሳዛኝም ነበር።መላ ምቱ “አሸናፊ ሁለትና ከዛ በላይ መጽሐፍ በየዓመቱ የሚጽፈው ፈንድ የሚያደርጉለት ድርጅቶች ስላሉ ነው።” የሚል መሆኑ ከማስገረም አልፎ ያሳዝናል፡፡ በወቅቱ ከማኅበሩ የቁርጥ ቀን ልጆች ይህን ስንሰማ በጣም ነበር የተገረምነው። ምክንያቱም የመጽሐፍ ማሳተሚያ ዋጋ በፈንድ ሊገኝ ይችል ይሆናል። ጸጋ እንዴት በፈንድ ሊገኝ ይችላል? ለሚለው ጥያቄ መልስ የሚሰጠን አካል ማግኘት ባለመቻላችን ነው። የጽሑፍ ጸጋ በገንዘብ እንደሚገኝ “የደረሰበት” ማኅበረ ቅዱሳን ምን ያህል የሚያደርጉትንም የሚያወሩትንም በማያውቁ ሰዎች የተሞላ መሆኑን ያሳየ ነበር።
ከነዚህ ሁሉ ሙከራዎች በኋላ ግን ማኅበሩ ዲ/ን አሸናፊን በከፍተኛ ጥላቻ መከታተል የጀመረው ከአቡነ ጳውሎስ ጋር ተቀራረበ የሚል ወሬ ከተሰማ በኌላ ነበር። ከእሳቸው ጋር መቀራረብ ወንጀል ሆኖ የክስ ፋይል ያቀረበው ማኅበረ ቅዱሳን ፈጽሞ የቤተ ክርስቲያንን ሥርዓት የማያውቅ በቤተ ክርስቲያን ሥርዓት የሚያስወግዝና የማያስወግዝን ነገር ያላወቀና ጥላቻ ብቻውን ለውግዘት ምክንያት ይሆናል ያሰኘ ነበር። ቤተ ክርስቲያን አባት የላትም ብሏል። ምዕመናን ተችቷል የመንግሥት ባለስልጣናትን ወቅሷል የሚል የውግዘት አንቀጽ በዓለም ቤተ ክርስቲያን ታሪክ የመጀመሪያው እና በዲ/ን አሸናፊ ላይ ብቻ የተፈጸመ  መሆኑን ያሳየ ነበር።
ከዓመት በፊት በብጹዕ አቡነ ገሪማ ፊርማ የዲያቆን አሸናፊ መጻሕፍት ለሊቃውንት ጉባኤው ለመምሪያው ሥራ አገልግሎት እንድታውሉት ታዟል ተብለው የተላኩ ሲሆን አሁን ደግሞ በዚያው ሊቃውንት ጉባኤ በኩል ተግሣጽና ምክር ያስወግዛል የሚል ጽሑፍ መውጣቱ አስገርሟል። 
 የአቡነ ገሪማ ደብዳቤን ለማንበብ ይህንን ይጫኑ
በዘንድሮው የሲኖዶስ ስብሰባ ዲያቆኑን ከቅዱስነታቸው መለየት የሚል ትእዛዝ ከማኅበረ ቅዱሳን ተሰጥቷቸው የገቡት ጳጳሳት ገና ስሙ ሲጠራ ጀምሮ ይወገዝልን እያሉ መጮኻቸው ተሰምቷል። ኃጢአቱን አበዛሁ ብለው የእርሱ ምንፍቅና ልዩ ነው ተብለው የተናገሩት አቡነ አብርሃም ወወገዝ አለበት “ኢየሱስ ዋናችን ነው እኮ ነው ያለው” ሲሉ ተደምጠዋል። ኢየሱስ ዋናችን ነው ማለት ለውግዘት እንደ መከራከሪያ መቅረቡ ልብን የሚያደማ ምክንያት ሆኖ አልፏል።
ሲኖዶሱ ስለውግዘቱ በሚከራከርበት ጊዜ በሊቃውንት ጉባኤም ሆነ በሲኖዶሱ ተጠርቶ እንዲወገዝ ያልተጠየቀው ዲ/ን አሸናፊ ፍትሕ እንዲታይልኝ ስለመጠየቅ ሲል ተጠርቼ ልጠየቅ የሚል ደብዳቤ ለሲኖዶሱ አስገባ። ይህ ደብዳቤ በገባ ጊዜ ቅዱስ ፓትርያርኩ እንዲህ የሚል ደብዳቤ መጥቷል ብለው ደብዳቤውን ካነበቡ በኌላ “እንደ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ልጆቹ ፍትሕ ሊታይላቸው ይገባል ተጠርተው ይጠየቁ” ቢሉም እነ አቡነ አብርሃም፣ አቡነ ዲዮስቆሮስና እና አቡነ ሳሙኤል በፍጹም ሊጠየቁ አይገባም። ማኅበረ ቅዱሳን ባጠናው መሠረት ዝም ብሎ ማውገዝ ነው ሲሉ ተከራክረዋል። ተዉ ሲባሉም በቃ ይወገዙና ይቅርታ ይጠይቁ የሚል ተራ መከራከርያ አቅርበው ለማስወገዝ ተንቀሳቅሰዋል፡፡
የሲኖዶሱ ስብሰባ ሊያልቅ ሲል እነማን ይወገዙ የሚለው አጀንዳ አንደገና ተነሥቶ የነበረ ሲሆን የዲ/ን አሸናፊ ስም ሲጠራ እነ አቡነ ገሪማ ጠንካራ ተቃውሞ በማቅረባቸው እና እንኳን ፍትህ ይታይልኝ ብሎ ጠይቆ እና ባይጠይቅም እሱን ማስወገዝ የሚችል ማስረጃ አልቀረበም በማለታቸው የእርሱ ጉዳይ እንደገና እንዲታይ ተብሎ ታልፎ ነበር፡፡ ይህን የተረዳችው ደጀ ሰላምም የውግዘቱን በተመለከተ የሲኖዶሱን ውሳኔ ስትዘግብ የዲያቆን አሸናፊን ስም ሳትጠቅስ አልፋለች፡፡
ነገሩ ሁሉ አልቆ ቃለ ጉባኤው ሲዘጋጅም በሲኖዶሱ ይወገዝ ስላልተባለ ከተወጋዞች መሐል የዲያቆን አሸናፊ ስም ሳይካተት ቃለ ጉባኤው ከተፈረመ በኌላ አቡነ ቀውስጦስ ውሳኔውን ሊያስባርኩ ወደ ማኅበረ ቅዱሳን ቢሮ ይዘው ሲሄዱ የአሸናፊ ስም አለመኖሩን ያስተዋሉት የማኅበሩ ሰዎች ከተቻለ የአሸናፊ ስም እንዲገባ ለማድረግ ይሞክሩ ብለው በመጠየቃቸው አቡነ ቀውስጦስ ከሲኖዶሱ ጸሐፊ ጋራ ዱላ ቀረሽ ክርክር አድርገው ስሙ በእስኪርቢቶ እንዲጻፍ አስደርገዋል፡፡
ሰነዱ ከተፈረመ በኌላ የዲ/ን አሸናፊ ስም በእስኪርብቶ ተጽፎ መካተቱ ያሳሰባቸው የማኅበሩ ሰዎች የሰነዱ ገጽ 38 እንደገና ተጽፎ እንዲወጣ አስደርገው በየጳጳሳቱ ቤት እየተሯሯጡ አስፈርመዋል፡፡ ነገር ግን ሁለተኛው ፊርማ የተፈረመው ጳጳሳቱ ወደ ሀገረ ስብከታቸው መሄድ ከጀመሩ በኌላ ስለሆነ በመጀመሪያው ፊርማ የተገኙ ጳጳሳትን ማግኘት ሳይችሉ ቀርተዋል፡፡ ለዚህም ማስረጃው በሁለቱ ሰነዶች ላይ የፈረሙት ጳጳሳት ቁጥር መበላለጥ ነው፡፡ በመጀመሪያው እና በሲኖዶሱ ውሳኔ መሠረት በተዘጋጀው ሰነድ የዲያቆን አሸናፊ ስም የሌለበት ሲሆን የፈረሙትም ጳጳሳት ቁጥር 29 ነው፡፡ በሁለተኛው እና በማኅበረ ቅዱሳን ፍላጎት መሠረት የዲያቆን አሸናፊ ስም ተካቶበት ፕሪንት በተደረገው ሰነድ ላይ ደግሞ የፈረሙት ጳጳሳት ቁጥር 18 ነው፡፡ ይህም ማኅበሩ ምን ያህል በሲኖዶሱ ሥራ ጣልቃ እንደገባና ጳጳሳቱንም እንደፈለገ እንደሚያሽከረክራቸው ያሳያል፡፡ አንባቢ አይቶ እንዲፈርድ ሁለቱንም ገጽ 38 ሰነዶች አያይዘናል፡፡
ይህን ሲጫኑ ሰነዶቹን ያገኛሉ።  
በእንዲህ ያለ ሁኔታ በዓለማዊ ፍርድ ቤት እንኳ ተደርጎ የማይታወቅ ድርጊት በሲኖዶሱ የተፈጸመ ሲሆን ዓለማዊ ፍርድ ቤት እንኳን ዳኝነትን በከሳሽ ድምጽ ብቻ አያይም። በከሳሽ ክስ ብቻ ሊታይ የሚችለውም ተከሳሽ ተጠርቶ አልቀርብ ካለ ብቻ ነው። ዲያቆን አሸናፊ ግን ተጠርቶ ሳይጠራ ክሱ መታየቱ ሳያንስ አረ ልጠየቅ ብሎ አቤቱታ ቢያቀርብም የሲኖዶሱ አባላት እምቢኝ ማለታቸው ብዙዎችን አስገርሞአል። እንዲህ ያለውን  አሠራር በመታዘባቸውም ሲኖዶሱ የጫኑት ቆብ ክብርና የተሸከሙትን ኃላፊነት ከባድነት ያላገነዘቡ ሰዎች ስብስብ ሆኗል  ያሉ ታዛቢዎች በርካቶች ናቸው።
ሲኖዶሱ የተከሰሱትን ሰዎች ጠርቶ ለማነጋገር አለመወሰኑ ከፍተኛ ስህተት ነው። ሊቃውንት ጉባኤውም ከሁለት ሰዎች ውጭ ማንንም ሰው አለመማነጋገሩ አስገርሟል። ያነጋገራቸውንም ሁለት ሰዎች ነጻ አውጥቷል። ሌሎችንም ጠርቶ ቢያነጋግር ከብዙ ታሪካዊ ስህተቶች ይድኑ ነበር። ሁሉም ነጻ ይወጡ ነበር ባንልም በርግጥም ግን እንደ ዲያቆን አሸናፊ ያሉ አገልጋዮች ግን ከተከሰሱበት ሰነድ አንጻር አንዳችም ሊያስወግዛቸው የማይችል ሰዎች ነበሩበት።
አንዳንዶቹ ተከሳሾች ለምን እራሱ እንደተካተቱ አልገባንም። ምክንያቱም ከቤተክርስቲያን ከወጡ ብዙ ጊዜ የነበራቸው እና እንኳን ኦርቶዶክሳሚ ነን ሊሉ አይደለም አሁን የቤተክርስቲያኒቱ ስም ሲጠራ እራሱ የሚያጥወለውላቸው ናቸው። ኦርቶዶክሳዊ አይደለንም ያሉ ሰዎችን ኦርቶዶክሳዊ ናችሁ ብሎ በግድ ማውገዝ ንጹሐኑን የቤተክርስቲያን ልጆች እነ አባ ሰረቀን እነ መጋቢ ሐዲስ በጋሻው እና እነ ዲ/ን አሸናፊን የመሳሰሉትን ቀላቅሎ ለማስወገዝ ካልሆነ በቀር ፍይዳው አልታየንም።
ሌሎቹ ደግሞ እንዲያውም ከመሰረታቸው ፕሮቴስታንት የሆኑ በዚህች ቤተክርሰቲያን ውስጥ በምንም አይነት አገልግሎት ያላለፉ ስለኦርቶዶክሳዊት ቤተክርሰቲያንም በቂ ግንዛቤ የሌላቸውን ሰዎች በስማ በለው ማውገዝ ቤተክርስቲያኒቱንም ትዝብት ላይ የሚጥል ነው። ያልወለዱትን ልጅ በግድ ልጄ ነህ ልጅነትህን ሰርዣለሁ ማለትስ ይቻላል ወይ? እግዚአብሔር ይሰውረን እንጂ ጫን ብለውም ከከሰሱንም ውጤቱ አሳፋሪ ነው። ሲኖዶሱ በሰውም በእግዚአብሔርም ፊት ተጠያቂ ከመሆን አይድንም የምንለውም ለዚህ ነው። ማኅበረ ቅዱሳን ሰባት ሰዎችን አውግዙልኝ ብሎ ጠይቆ 9 ሰዎችን መርቆ ማውገዝስ ምን ይባላል?
እግረ መንገዳችንን ይህንን ጉዳይ አነሳን እንጂ እኛም ሆነ በርካታው ምዕመን አሁንም ፈጽሞ ሊወገዙ አይገባም ከምንላቸው ሰዎች መካከል ዋነኛው ዲያቆን አሸናፊ ነው። ለዚህም የደረሱን የኢሜል መልዕክቶች በቂ ማስረጃዎች ናቸው። የሄደውን ሁሉ ለምኖ ማምጣት የሚገባት ቤተክርስቲያን በልጆችዋ መጨከንዋ አስደናቂ ነው። ጳጳሳቱ ለይስሙላ እንኳ እነማን ናችሁ? እስኪ እንስማችሁ? ለማለት አለመድፈራቸው የተሸከሙት የአባትነት ሥልጣን ገብቷቸዋል ወይ? ያሰኛል። አለማውያን ፖለቲከኞች እንኳ የማይሰሩትን ስህተት ለመፈጸምስ እንዴት ደፈሩ? ለሚለው ጥያቄ ታሪክና ትውልድ ወደ ፊት መልስ ይሰጡበት ይሆናል።
ከውግዘቱ በኌላም ዲያቆን አሸናፊ አቤቱታዬን ለሰማይ ጌታ፣ ለምድር አባቶቼ ለማሰማት የሚል ርዕስ ያለው አቤቱታ አቅርቧል። በግንቦት 15/ 2004 ዓ.ም ቅዱስ ሲኖዶስ ባስተላለፈው የውግዘት ቃል ከልቤ አዝኛለሁ:: በሚል ዐረፍተ ነገር የሚጀምረው ይህ ደብዳቤ “በር ከፍተን ሰው ማስገባት በሚገባን ጊዜ በር ከፍተን ማስወጣት ጥቅሙ አልታይ ብሎኝ፣ እናት ቤተ ክርስቲያን የተሳሳተም ካለ በፍቅርና በምክር የመመለስ አቅሟን ጥላ ውግዘትና የይከሰሱልኝ ውሳኔ ማሳለፏ አሳዝኖኛል:: ባሳለፍኩት ዘመኔ ሁሉንም ለመውደድ እንጂ ማንንም ለመጥላት አልኖርኩም። አንዱን ቀድሼ ሌላውን አርክሼ ለመጻፍም አልተጋሁም። የተጋሁት የሰው ልጆች የሚጽናኑበትንና ሕይወትን አቻችለው የሚኖሩበትን ምክር ለመስጠት ነው። ይህንንም የሚከሱኝ እንኳ ደግመው ቢያስቡት የሚስቱት አይደለም:: በዚህች አገር ላይ የሚወገዙ መጻሕፍት ጠፍተው የእኔ መጻሕፍት መወገዛቸው ገርሞኛል:: አባቶችን ስም ጠርተው፣ ቆብ አውልቀው የተሳደቡ መጻሕፍት እያሉ ተግሣጽ እንደ ኑፋቄ፣ ታሪክ እንደ ሃይማኖት፣ ቀኖና እንደ ዶግማ ተቆጥሮ መወገዜ ደንቆኛል:: ደግሞም የተከሰስኩበትን ማለቴም ይሁን አለማለቴ ቀርቤ ሳልጠየቅ ክሴንም ፍርዱንም በጋዜጣ በመስማቴ በአገሬ ጭምር እንዳዝን አድርጎኛል።” እያለ ይቀጥላል።
ተጠርቶ ሳይጠየቅ የእምነት ክህደት ቃል ሳያሰማ አንዲያው በደፈናው ሥጋውያን እንኳ  የማይፈጽሙትን ስህተት ሲኖዶሱ መወሰኑ እንዳሳዘነው ይገልጥና በመቀጠልም በመሠረቱ ማኅበረ ቅዱሳን ባቀረበው የክስ አሳብ መወገዝ ቀርቶ መጠየቅ እንደሌለብኝ አምናለሁ:: ምክንያቱም ማኅበሩ የውንጀላ ዝርዝሩን ያቀረበው በጥቅምት 2004 ዓ.ም ሲሆን አስቀድሞ ከየካቲት 2003 ዓ.ም ጀምሮ ራሱ አውግዞን መጽሐፍ ጽፏል፣ ሲዲ አሰራጭቷል፣ የግንዛቤ ማስጨበጫ በማለት እርዳታ አሰባስቧል። የማይጨው ዘመቻ ዝግጅት እስኪመስል እያለቀሰ አስፎክሯል:: ስለሆነም ማኅበረ ቅዱሳን የውግዘት ሰነዱን ለሲኖዶሱ ያቀረበው አጽድቁልኝ ብሎ ነው። ማኅበረ ቅዱሳን መብቱ ስህተት ካለ ጥቆማ ማድረግ እንጂ ውሳኔ ማስተላለፍ አይደለም:: ለምን ይህን አደረግህ? ያለው ወገን ግን አልነበረም:: ቅዱስነትዎ በሰጡት ስህተትን የመለየት የቀኖና አካሄድና ማንም ማንንም በግሉ ተነሣሽነት መናፍቅ ማለት አይገባም በሚለው መመሪያ መንገድ ካጣ በኋላ ለጥቅምት 2004 ዓ.ም አውግዙልኝ ብሎ አቅርቧል:: በማኅበረ ቅዱሳን ያን ያህል አላዝንም። ኢትዮጵያውያን ወንድሞቼም እንደሆኑ እንጂ እንደ ባዕድ አላያቸውም:: ቅዱስ ሲኖዶስ ግን የቀደሙት አባቶች ለአርዮስ እንኳ የሰጡትን ዕድል ለእኔ በመከልከሉ በጣም አዝኛለሁ::” ሲል ሀዘኔታውን ይገልጣል።
“ክሱን ሳልሰማ ፍርዱን በመስማቴ በመገረም አዝኛለሁ::” የሚለው ዲያቆኑ ወረድ ብሎም የቤተ ክርስቲያኒቱን መጻሕፍትና ሥርዓት እየጠቀሰ ውግዘቱ ስህተት መሆኑን ይሞግታል፡-
 “በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ ፭ “ኢይስዓር ወኢያውግዝ ዘእንበለ ርትዕ ወለእመ አሰረ ወአውገዘ ዘእንበለ ርትዕ ውእቱኒ ይከውን እሱረ ወውጉዘ” ይህም ማለት “በማይገባ አይሰር፣ አያውግዝ፤ በማይገባ ቢያስርና ቢያወግዝ እርሱ ራሱ የታሰረና የተወገዘ ይሆናል፡፡” ይላል፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅም “ወኢንመልሕ ሰይፈ በላዕሌክሙ። አላ ናስተሐምም ለመድኀኒትክሙ” “እንድትድኑ ወደን እንታገሣችኋለን እንጂ በእናንተ ላይ ቸኩለን ሰይፋችንን አንመዝም (ፈጥነን ውጉዛን አንላችሁም)” ብሏል (ተግሣጽ ፬)፡፡
የቀደሙት አባቶች አንድን በኑፋቄ የተጠረጠረ ሰው ከማውገዛቸው በፊት አስቀድመው አነጋግረው መክረው፣ ገሥጸው እንቢ ካለ የማሰቢያ ጊዜ ሰጥተው ከብዙ ትዕግሥት በኋላ ሱባኤ ገብተው ያወግዛሉ፡፡ ለዚህም ሠለስቱ ምእት አርዮስን ጥፋተኛ ሆኖ በተገኘ ጊዜ ከማውገዛቸው በፊት ከመስከረም 21 - ኅዳር 9 ሱባኤ ገብተዋል እንጂ ሳናወግዝ አንለያይም አላሉም፡፡ ይህም የሚያሳየን ውግዘት ብዙ ትዕግሥትና ጸሎት እንደሚፈልግ ነው፡፡ (አባ ጎርጎርዮስ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ በዓለም መድረክ ምዕራፍ ፮)፡፡     
ዓለም አቀፋዊ በሆኑት በኒቅያ፣ በቁስጥንጥንያና በኤፌሶን ጉባኤዎች እንዲሁም በአገራችን  በጎንደር፣ በቦሩ ሜዳ በተደረጉ ሃይማኖታዊ ጉባኤዎች የተጠረጠሩ ተጠይቀው ተከራክረው፣ ተረትተውና አልመለስም ሲሉ የመለየት ሥራ ይሠራ ነበር።
ከሁሉ በላይ ደግሞ ጌታችን ለቤተ ክርስቲያን የሰጣት ስሕተትን የመለየት መንገድ፡- “ወንድምህም ቢበድልህ፥ ሄደህ አንተና እርሱ ብቻችሁን ሆናችሁ ውቀሰው። ቢሰማህ፥ ወንድምህን ገንዘብ አደረግኸው፤ ባይሰማህ ግን፥ በሁለት ወይም በሦስት ምስክር አፍ ነገር ሁሉ እንዲጸና፥ ዳግመኛ አንድ ወይም ሁለት ከአንተ ጋር ውሰድ፤ እነርሱንም ባይሰማ፥ ለቤተ ክርስቲያን ንገራት፤ ደግሞም ቤተ ክርስቲያንን ባይሰማት፥ እንደ አረመኔና እንደ ቀራጭ ይሁንልህ።” የሚል ነው፡፡ (ማቴ. 18፥15-17)፡፡  
ከሚሉት የቤተክርሰቲያን አውነቶች አንዱንም ያልፈጸመ ሲኖዶስ እራሱን ይታዘብ ዘንድ ከረዳው ማስረጃዎችን ማስቀመጡ ጥሩ ነው።
“የቤተ ክርስቲያን ትልቅ ድሏ ማውገዝ ሳይሆን የተሳሳተም ካለ መክሮ መመለስ ነው:: ቤተ ክርስቲያን በማንም መጥፋት ደስተኛ አይደለችም:: የቤተ ክርስቲያን ራስ ክርስቶስም ዘጠና ዘጠኝ በጎችን ትቶ አንዱን ፍለጋ የመጣ ነው። ያሉኝ ብዙ ናቸው የጠፋችው አንዲት በግ ናት ብሎ አልናቃትም፡፡ ለጠፉትም ግድ ይለዋል።” ብሎ የጻፈው ዲያቆን አሸናፊ ቅዱስ ፓትርያርኩም ቢሆን ጊዜው ቢያልፋቸው ታሪክና እግዚአብሔር ግን እንደማያልፉአቸው እንዲህ ሲል ይገልጻል።  “ ቅዱስነትዎም ይህንን የጌታችንን መንገድና የኖረውን ቀኖና የማስጠበቅ ኃላፊነት እያለብዎ ከቀኖና ውጭ ውግዘት በመተላለፉም በታሪክና በእግዚአብሔር ፊት ይጠየቃሉ::”
ዲያቆን አሸናፊ ሀሳቡን ሲጠቀልልም እንዲህ በማለት ነው፡- በጥቅሉ የተላለፈው ውግዘት ሕገ ቤተ ክርስቲያንን (ፍትሕ መንፈሳዊን)፣ የሦስቱን ዓለም አቀፍ ጉባኤዎች አሠራር፣ የአገራችንን የኖረውን አካሄድ፣ የቅዱስነትዎን መመሪያ፣ ከሁሉም በላይ ደግሞ የጌታችንን ትምህርት የተቃረነ ውግዘት ሆኖ ተሰምቶኛል፡፡
በተከሰስኩበት ጉዳይና እናንተን አባቶቼን ያሳዘነ ነገር ካለ ክሱ ሲደርሰኝ ዝርዝር መልስ በማቅረብ አስረዳለሁ ብዬ አምናለሁ:: በግርድፉ እንደምሰማውና በአንዳንድ መገናኛ ብዙኃን እንደተገለጠው በጥቅሉ አስተያየቴ፡-
  1. እኔ ልጠየቅ የምችለው በስሜ በተጻፉ 16 መጻሕፍት ብቻ በመሆኑ በስሜ ባልተጻፉ መጻሕፍት መከሰሴን እቃወማለሁ። በእነዚህ መጻሕፍት ውስጥም ለተዋህዶ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያኔ ከመቆርቆር ውጭ ስሟን የሚያጎድፍ ነገር አልጻፍኩም።
  2. አንቀጸ ብርሃን የሚባል ድርጅት አለው ተብሎ በመነገሩ እንዲህ የሚባል ድርጅት የሌለኝ ሲሆን የተወገዘውም የሌለ ድርጅት መሆኑን እገልጣለሁ።
  3. አንቀጸ ብርሃን በሚባል ድርጅት ውስጥ አባል የሆነ ተብሎ የተጠቀሰው ዳንኤል ተሾመ የተባለውን ሰው ከአሁን በፊት ስሙንም ሰምቼ የማላውቀው በሌለኝ ድርጅት ውስጥ የሌለኝ ሠራተኛዬ በመሆኑ አሳቡን በጽኑ እቃወማለሁ:: እንዲታረም ስልም በብርቱ እጠይቃለሁ። ይህም የሚያውቁኝን ሁሉ ያሳዘነ መሆኑን እገልጣለሁ::
እኔም አስቀድሜ ማመልከቻዬን ለቅዱስ ሲኖዶስ ያቀረብኩት በአባትና ልጅ መንፈስ እንድንግባባ ነበር:: ነገር ግን አናናግርም ተብዬ በመመለሴ ፈቃዳችሁን አከብራለሁ:: ፍጹማን የሆኑ መጻሕፍትን ጽፌአለሁ ባልልም ብዙ ብፁዓን አባቶችም አንብበው እንዳደነቁ ከእርስዎም የተሰወረ አይደለም:: እውነት እስክታበራም እጠብቃለሁ:: የቅዱስነትዎንና የብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳትን ጤንነትን እመኛለሁ::” ብሏል።
የዲያቆን አሸናፊን ውግዘት ከማኅበረ ቅዱሳን አባላት ጀምሮ በርካታ ሰዎች የተቃወሙት ሲሆን ከሌሎቹ ተወጋዞች በተለይ የእርሱ ጉዳይ አሁንም እያነጋገረ ይገኛል። የማኅበሩ ዋና የሆኑት እነ ካሳሁን ቀርቦ ለጠየቃቸው ሰው የእርሱ ጉዳይ እኛን አይመለከተንም ለማለት ቢሞክሩም በሥራ አመራርነት ያሉበት ማኅበር ያስገባው የይወገዝልን ጽሑፍ እኔን አይመለከተኝም ማለት አስቂኝ ነገር ነው የሚሆነው።
በምቀኝነቱ ወደር ያልተገኘለት ማኅበረ ቅዱሳን የዲያቆኑ መጻሕፍት በከፍተኛ ደረጃ መሸጥ እንቅልፍ ነሥቶት ከገበያ ለማውጣት ያደረጉት ሙከራ ተሳክቶልኛል ብሎ ቢያምንም መጻሕፍቱ ግን አሁንም በሕዝቡ ዘንድ ያላቸው ተቀባይነት ሰፊ ስለሆነ ሽያጫቸው እንዳልተቋረጠ ለማወቅ ተችሏል፡፡ በመንፈስ ቅዱስ ሀሳብ ሳይሆን በገበያ ሕግ ለሚመራ ማኅበር እንዲህ ያለው ነገር ስኬት ቢመስለውም ከላይ የሆነን ጸጋ ማቋረጥ ስለማይቻል ዓለማዊ መጻሕፍት ቤቶች እንኳ መጻሕፍቱን በስፋት መያዝ ከጀመሩ ሰንብተዋል፡፡
የፕሮቴስታንት ጸሐፊዎችን ጨምሮ የሌሎችን ሰዎች መጽሐፍ እየገለበጠ እና ሀሳብ እያሳጠረ የሚያሳትመው ማኅበረ ቅዱሳን (ስለቤተ ክርስቲያንህን እወቅ መጽሐፍ የጻፍነውን ይመልከቱ፡፡ ወደፊትም ከፕሮቴስታንት መጽሐፍ ተገልብጠው በማኅበሩ ሰዎች የታተሙትን መጻሕፍት ከነማስረጃው እናቀርባለን፡፡) በያረጋል አበጋዝ አማካኝነት የዲያቆኑን ጸጋ መቀበል ስለከበደው መጽሐፍቱ የፕሮቴስታንት መጽሐፍ ቅጂ ናቸው ማለቱም ይታወሳል፡፡ ከእነዚህ እንዳይል ግን ከተራ የስም ማጥፋት ዘመቻ የዘለለ ነገር ስላልነበር ማስረጃ ማቅረብ አልቻለም፡፡ ወደፊትም መቸም ቢሆን ሊያቀርብበት አይችልም፡፡ ክሱ ግራ የገባቸው መጻሕፍትን መጻፍ የጀመሩትን ፕሮቴስታንቶች እንዲህ ያሉትን መጽሐፍት ጽፈዋል ብለው የማይገባቸውን ክብር ለመስጠትና ዲያቆኑን ለማሳነስ የሞከረ ክስ ቢሆንም እንዲህ ብለው ከተናገሩት እና ከጻፉት የማኅበሩ ሰዎች ጀምሮ አንባቢዎቹ ሁሉ ዲ/ን አሸናፊ በጸጋ እንጂ በኩረጃ የእግዚአብሔርን ሥራ እንደማይሠራ ጠንቅቀው ያውቃሉ፡፡ ገለበጠ ሲሉ የከረሙት የማኅበሩ ሰዎች መለስ ብለው ደግሞ ለእገሌ ለእገሌ እና ለእገሌ መጽሐፍ የሚጽፍላቸው እሱ ነው ሲሉ እርስ በእርስ የሚጋጭ ሀሳብም አስነብበውናል፡፡
በቤተ ክርስቲያናችን ታሪክ በልጅነቱ በርካታ መጽሐፍትን በመጻፍ በሕዝቡ ዘንድ ከፍተኛ ተቀባይነት ያገኘው ዲያቆን አሸናፊ መኮንን በእውነት እግዚአብሔር በእርሱ እንደሚሠራ ከሚያሳዩት ምልክቶች አንዱ በመጽሐፉ ተለውጠው ወደ ቤተ ክርስቲያን የተመለሱ የሕይወት አቅጣጫቸውን ያስተካከሉ እግዚአብሔር ዓላማዬ ያሉ ሰዎችን ምስክርነት ስንሰማ ነው። እራሱን ላጣ ሰው እራስን መፈተሻ  ተስፋ ለቆረጠ ሰው ከእግዚአብሔር የሆነውን ተስፋ የሚቀጥልበትን መንገድ የሚጠቁሙ መሆናቸው የተመሰከረላቸው የዲያቆን አሸናፊ መጻሕፍት ማኅበረ ቅዱሳንን እራሱ እንደተናገረው መጻሕፍቶቹን በሀገሪቱ ውስጥ ያሉ ሰንበት ትምህርት ቤቶች የሥነ ምግባር መመሪያ አድርገው እስኪቀበሉት ደረስ ተቀባይነታቸው እጅግ ሰፍቷል።
ዲያቆን አሸናፊ ምክር ለወዳጅ በሚለው መጽሐፉ እንዲህ የሚል ምክር ለወዳጆቹ አስቀምጦ ነበር፡፡
ወዳጄ ሆይ
አማኒ እንጂ አክራሪ አትሁን፡፡ አማኒ ያመነውን የሚኖር በፍቅርም የሚማርክ ጀግና ነው፡፡ አክራሪ ግን ጥቂት እውቀቱን ከዱላ ጋር ለማስከበር የሚሞክር ነው፡፡ የከረረ ነገር መበጠሱ አይቀርም፡፡ የከረረ ነገር ሲከርም ሲበጠስም ስጋት ነው፡፡ አክራሪነት የዓለሙ ልከኛ ሰው እኔ ነኝ፡፡ ከእኔ በቀር በዓለም ላይ ማንም መኖር የለበትም፡፡ ከምሥራቅ ስገላበጥ ምዕራብ እደርሳለሁ፡፡ ከሰሜን ስራመድ በአንድ ስንዝር ደቡብን እረግጣለሁ፡፡ ስለዚህ ከእኔ ውጭ ማንም መኖር የለበትም ብሎ እንደ ማሰብ ነው፡፡ የአክራሪነት ምንጩ ድንቍርና ነው፡፡ አክራሪ ሰው በከሳሽነት መንፈስ የተያዘ እንጂ የሚያሳየው ማራኪ ሥራ የሌለው ነው፡፡ ጥቂት እውቀቱ ከሰፋች የካደ ስለሚመስለው ላለማወቅ ተጠንቅቆ የሚጓዝ ነው፡፡ እርሱ ካለበት ጉድጓድ ውጭ ዓለም ያለ የማይመስለው፣ ካለመድኩት መንፈስ ቅዱስ የለመድኩት ሰይጣን ይሻላል ብሎ ከመቃብር ጋር በኪዳን የሚኖር፣ ተስፋ የሌለው፣ ሳይሞት መኖር ያቆመ፣ ሳይቀበር እውቀትን የጨረሰ ሰው ነው፡፡ የአክራሪነት ወንድሙ ድርቅና ነው፡፡ እኔ ያወኩት ብቻ ትክክል፣ እኔ ከሰማሁት ውጭ ያለው ያልተነገረ ነው፣ ዓለም በእኔ ጓዳ በኩል ነው የምታልፈው፣ እኔ ያልገባኝ ነገር እንዴት ልክ ይሆናል? ብሎ የሚያስብ ነው፡፡ መሃይም ማለት ያልተማረ ሳይሆን መማር የማይፈልግ ነው፡፡ የሰይጣን ትልቅ ግዛቱ ድንቁርና ነው፡፡ ሰዎች የኅሊና ዓይናቸውን ካላሳወረ በቀር አያመልኩትምና  ኅሊናቸውን ያጨልማል፡፡ ጓዴ ሆይ፡- ማወቅን እንደ ጨረሰ ሰው የምትኖር ከሆነ መኖርህ ምክንያት አልባ መሆኑን አስብ፡፡ ባለህበት ጉድጓድ መጠን ሁሉንም ነገር ካየኸው ሁሉም ነገር ይጠብብሃል፡፡ ላንተ ይጠብብሃል፡፡ ዓለም ግን ሰፊ እንደሆነ ይቀጥላል፡፡
ወዳጄ ሆይ
የማይማር መንፈስ አደገኛ መሆኑን እወቅ፡፡  ትንሽ እውቀትም የሥጋ  ኅይልን ይሻልና እውቀትህን አሟላው፡፡ አንድ ምሳሌ ልንገርህ፡- በጉልበቱ እያስፈራራ ከደጀ ሰላም የሚበላ አንድ ወጠምሻ ሰው ነበር፡፡ የሌሊቱን ቁመት ሳይቆም፣ ደግሞም ቅዳሴ ሳይቀድስ ያለፋበትን እንጀራ በመብላቱ ቀሳውስቱ ሁልጊዜ ቢያጕረመርሙም ማንም ደፍሮ የከለከለው ግን አልነበረም፡፡ እርሱም ያልተማረ እንደሚሉት ስለሚሰማ እማራለሁ ብሎ ወደ አንድ መምህር ሄዶ፡- አባቴ ዳዊት አስደግሙኝ ብሎ ይጠይቃቸዋል፡፡ እርሳቸውም አንተ ተማር እንጂ እኔ ምን ከብዶኝ? ብለው በደስታ  እሺ ብለው ማስተማር ጀመሩ፡፡ እርሱም መዝሙረ ዳዊት ምዕራፍ አንድ ፍካሬን በደንብ እንደ ቻለ በቃኝ አላቸው፡፡ እርሳቸውም ገና ነው እኮ ቢሉት፡- አይ አባቴ ይህቺ ፍካሬ ከዱላዬ ጋር ትበቃኛለች አላቸው ይባላል፡፡ ዛሬም ከዱላዬ ጋር ፍካሬ ትንሽ እውቀቴ ትበቃኛለች ብለው የሚኖሩ ብዙዎች ናቸው፡፡ አንተ ግን እንደ እነርሱ አትሁን፡፡
ወዳጄ ሆይ
አትክልት በከበረ ቦታ  ተቀምጦ ለመብል የሚቀርበው ከነልምላሜው ከምድር ሲነቀል ነው፡፡ አንተም በሰማይ የምትከብረው አምነህ ስትሞት፣ በትላንት ትዝ  ሳይሆን በዛሬ ሁነት ስትገኝ ነው፡፡ ጉዞውን በመንፈስ ጀምሮ በሥጋ የሚፈጽም እመሬት ላይ ለምልሞ እዚያው ደርቆ እንደሚቀር አትክልት ነውና ከነእምነትህ ከነምግባርህ እንድታልፍ ጸልይ፡፡
ወዳጄ ሆይ
ፈራጅ ሲያደርጉህ የሰውን ፊትና የነገን ጥቅምህን አስበህ ፍርድን አታጓድል፡፡ በሚፈርዱት የሚፈርደው ጌታ  ከበላይህ እንዳለ አስብ፡፡ ፍርድ ለተበዳይ ለበዳይ ሳይሆን እውነተኛ ፍርድ ለእግዚአብሔር ነውና፡፡ ደግሞም ቂመኛ በቀለኛ ስትሆን የዳኝነትን ሥራ አትምረጥ፡፡ ዳኝነት የሚባለው ራስን ማስከበሪያ ሳይሆን ወገንን መጥቀሚያ ነውና፡፡

7 comments:

  1. የዲ/ን አሸናፊ መጽሐፍት ለህይወቴ መቀየር ምክንያት ናቸው። መጽሐፍቱን ማንበብ በጣም ያረካል። ብዙ ጥያቄዎቼን አምላኬ በሱ መጽሐፍት በኩል መልሶልኛል። በጸጋ የሚጽፍ ሰው ለመሆኑ የኔ ሕይወት ምስክር ነው።

    ReplyDelete
  2. ለዲ/ን አሸናፊ መጻሕፍት እኔ ራሴ አንድ ምስክር ነኝ። በተለይ የኑሮ-መድኅን የሚለው መጽሐፍ። ወዳልሆነ አቅጣጫ እየተጓዝኩ ነበር፣ ግን እግዚአብሔር በዚህ በኩል ለሕይወቴ ደርሶላታል። እግዚአብሔር ይመስገን።
    ደግሞ መጽሐፉ ባልሳሳት በአራት ዓመት ውስጥ ሰባተኛ ጊዜ ታትሟል። ይህም ምን ያህል ተነባቢ እንደሆነ ያሳያል።
    እግዚአብሔር እየሰራበት ነው። የእግዚአብሔርን አሠራር ደግሞ ማንም ሊያግደው አይችልም።

    ReplyDelete
  3. D/n Ashu, you already did a miracle. i love all your books. they are sweet to the soul, and health to the bones. they are well-written and contained sound, practical advice. In fact, I have already benefitted from them.I am thankful for your wisdom. I know you are gonna shine more. God is working on your behalf. Keep trusting.
    Thank you and keep these good books coming.your brother in Christ.

    ReplyDelete
  4. his books are so good i am z witness

    ReplyDelete
  5. ashu i dont know u in person but i know ur books. ayzohe minem athonem
    bertehe zafe.

    ReplyDelete
  6. Yezihene leje mesehaf anebalu betureta edmeye mesenaga honewegal endihe yale cheger kederesebet asazage new. Yehine hono begegeroche tezenageto serawenmakom yelebetem berta lelew wedegalu.

    ReplyDelete
  7. አሹ ሕይወቴን አግዘሀል። እግዚአብሔር ረድቶህ ለነብሴ መጽናናት የሚሆኑ መጽሐፍትን ጽፈሀል። ለኔ በግል የተቀምከኝ ሰው ነህ። በአካል ባላውቅህም በመጽሐፍት ግን በደንብ አውቄሀለሁ። አይዞህ ከሰው የሆነው እዚሁ ምድር ቀሪ ነው። ያስነሳህን አምላክ አስብ።

    ReplyDelete