Saturday, March 31, 2012

ጋዜጠኞች ሆይ የጣላችሁትን ሚዛን አንሡ!


ጋዜጠኛነት ሊያሟላቸው ከሚገቡ የሙያ ሥነ ምግባራት መካከል አንዱ ሚዛናዊነት ነው፡፡ ጋዜጠኛ ሰው እንደ መሆኑ ራሱ የሚደግፈው ወይም የሚቃወመው ሐሳብ ሊኖር ቢችልም፣ የግል አቋሙን በዘገባው ውስጥ ሊያካትት እንደማይገባው የሙያው ሥነ ምግባር ያስገነዝባል፡፡ ይሁን እንጂ በአገራችን የጋዜጠኛነት ሙያ ብዙ ጊዜ ሚዛናዊነትን ሲጠብቅ አይታይም፡፡ አንዳንድ ሚዛናዊ ዘገባ የሚያቀርቡና ለሙያቸው ታማኝ የሆኑ ጋዜጠኞች ባይጠፉም፣ ብዙዎች ግን  የሚያቀርቧቸው ዘገባዎች ፍጹም ወገንተኛ የሆኑና የሙያውን ሥነ ምግባር የሚያፈርሱ ሆነው ይገኛሉ፡፡

በተለይም የነጻ ፕሬስ ውጤቶች የሆኑ ብዙዎቹ የግል ጋዜጦችና መጽሔቶች ነጻ ሆነው አለመገኘታቸውና እውነትን በሚዛናዊነት ከማቅረብ ይልቅ ወገንተኛነት የሚንጸባረቅባቸው መሆኑ የጋዜጠኛነትን ሙያ እጅግ እየጎዳው ነው፡፡ በዚህ አገር ነጻ ፕሬስ ማለትም መንግሥትን ወይም የታላላቅ ሃይማኖታውያን ተቋማት መሪዎችን በመቃወም መዘገብ ተደርጎ እየተወሰደ መሆኑ ሌላው የተዛባ የነጻ ፕሬስ አካሄድ ሆኗል፡፡ መንግሥትንም ሆነ የሃይማኖት ተቋማት መሪዎችን በተገቢው መንገድ ተችቶ መጻፍ አግባብነት ያለው አይደለም እያልኩ አይደለም፤ ነገር ግን ከጭፍን ጥላቻና ከጭፍን ድጋፍ የጸዳ ዘገባ ሊቀርብ ይገባል ነው ክርክሬ፡፡

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የግል ፕሬሶችን ሰፊ ሽፋን ይዘው የሚገኙት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዙሪያ የሚወጡ ዘገባዎች ናቸው፡፡ ለዜና ፍጆታ የሚውል ጉዳይ ከተገኘ መዘገቡ ትክክል ነው፡፡ በአዘጋገቡ ሁኔታ ግን በአብዛኛው የአንድን ወገን ሐሳብ ብቻ ደግፎና ሌላውን ተቃውሞ የመዘገብ ሁኔታ ነው የሚስተዋለው፡፡ ሚዛናዊት የሚባል የጋዜጠኛነት ሥነ ምግባር የሌለ እስኪመስል ድረስ፣ በጭፍን አንዱን ጻድቅ ሌላውን ኃጥእ፣ አንዱን ትክክል ሌላውን የተሳሳተ፣ አንዱን ለቤተ ክርስቲያን ተቆርቋሪ፣ ሌላውን ቤተ ክርስቲያን አፍራሽ፣ አንዱን ሃይማኖተኛ፣ ሌላውን መናፍቅ ብሎ የመፈረጁ አደገኛ አካሄድ ብዙ እያስተዛዘበ ይገኛል፡፡ ይህ የጋዜጠኛነትን ሙያ በእጅጉ እየተፈታተነ ያለ አደገኛ አካሄድ ነው ብዬም አስባለሁ፡፡

Wednesday, March 28, 2012

ማኅበረ ቅዱሳን ከሰሞኑ በሃይማኖት ሽፋን የአገራችንን የፖለቲካ አየር ለመበከል ያደረገው ጥረት እንዳልተሳካለት ተገለጸ


ፖለቲካዊና ሃይማኖታዊ መለያዎችን ለብሶ እንደአየሩ ሁኔታ ሲጫወት የቆየውና በዚህ በአቢይ ጾም ህዝቡ በተለይ ስለ ዝናብ እጥረት እግዚኦ እያለ ባለበት ወቅት ፖለቲካዊነቱ አይሎበት በተቃዋሚ ፖለቲከኛነት የተገለጠውና በሃይማኖት ሰበብ አገርን ለማመስና ኦርቶዶክሳውያንን በመንግስትና በቤተክህነት ላይ ለማነሳሳት ዘመቻ የጀመረው ማህበረ ቅዱሳን፣ በአሜሪካ የሚገኙ ካድሬዎቹን ከማሰለፍና በድረገጾቹ ላይ የጦርነት ነጋሪት ከመጎሰም ያለፈ ትርፍ እንዳላገኘ በአገር ውስጥ ያለው ሁኔታ ይመሰክራል።

በዋልድባ ገዳም አካባቢና የገዳሙ ይዞታ ባልሆነው ቦታ ላይ ሊሰራ የታቀደውን የስኳር ልማት ፕሮጀክት በመቃወምና በዝቋላ ተራራ ላይ ከበጋው ደረቅ የአየር ንብረት ጋር በተያያዘ የተነሳውን ሰደድ እሳት ምክንያት በማድረግ ክስተቶቹን ፖለቲካውን ለማስተዋወቅና ተከታይ ለማፍራት እየተጠቀመበት መሆኑን እየታዘብን ነው። በዋልድባ ገዳም ውስጥ ሰርገው ከገቡ የቀበሮ ባህታውያን ፖለቲከኞች ጋር ማህበሩ ያለውን ግንኙነት አሜሪካ ካሉት ወኪሎቹና ስውር አመራሮቹ ጋር በማቀናጀት የጀመረው ሰላማዊ ሰልፍ ብዙዎችን አስገርሟል። አንድአድርገን የተባለው የማህበረ ቅዱሳን ድረገጽ
“ዋልድባ ሲመታ  ዝቋላ አለቀሰ፣
እኔ አላማረኝም-ይሄ አገር ፈረሰ።
ዋልድባ ሲታመስ-ዝቋላም ነደደ፣
እኔ ፈርቻለሁ- ይሄ አገር ታረደ።”
በሚል ህዝቡን ለመቀሰቀስ የተጠቀመበት የክተት አዋጅ ማህበሩ በፖለቲካ መስከሩንና በዋልድባና በዝቋላ ስም አጋጣሚውን ለፖለቲካ ፍጆታው ለመጠቀም እየተራወጠ መሆኑን ያሳያል፡፡ በዋልድባ አካባቢ ሊሰራ ታቀደው የስኳር ልማት ፕሮጀክት የገዳሙን ክልል ያልነካ መሆኑን፣ ከገዳሙ ሰርጎገብ ፖለቲከኞችና ከማህበረ ቅዱሳን በቀር የገዳሙ መነኮሳት፣ የአካባቢው ተወላጆች፣ የመንግስት አካላትና የቤተክህነት ተወካዮች ባሉበት በተደረገ ውይይት የተረጋገጠ ነው፡፡ እውነቱ ይህ ሆኖ ሳለ በዋልድባ አካባቢ በመንግስት የታቀደው የልማት ስራ ቢሰራ “አገር ፈረሰ” ያሰኛል ወይ? ይህ አይን ያወጣ ፖለቲካ እንጂ ሃይማኖተኛነት አይደለም፡፡ ደግሞስ የዝቋላ ተራራ በበጋው የአየር ንብረት ሳቢያ ቢቃጠል “አገር ታረደ” ያሰኛል ወይ? መንግስት ተራራውን በማቃጠል ምን ይጠቀማል? በዚህ የሚያገኘው የፖለቲካ ትርፍ አል ብሎ ማሰብስ ይቻላል ወይ? ይህ በፍጹም የማይታሰብ ነገር ነው፡፡ እንደዚህ አይነት አደጋ በአገራችን ብቻም ሳይሆን በሌሎችም አገሮች ይከሰታል፡፡ አደጋው ተፈጥሮኣዊ እንጂ መንግስት ሆን ብሎ ያደረሰው ነው ማለት የማያስኬድ ነው፡፡ አሁን በአገራችን በአብዛኛው የበልግ ዝናብ እጥረት አለ፤ ሙቀቱም ከፍተኛ ነው። ለዚህም መንግስትን ተጠያቂ ሊሆን ነው? ይህ በጣም አስቂኝ ነው። ስለዚህ በሃይማኖት ካባ የምታደቡ ፖለቲከኞች ሆይ እጃችሁን ከቤተክርስቲያናችን ላይ በማንሳት በፖለቲካ መለያችሁ ብቻ ጨዋታውን ብትጫወቱ የተሻለ ነው።

Tuesday, March 27, 2012

"ማኅበረ ቅዱሳን" ከፍተኛ የፖለቲካ ኪሣራ ደረሰበት

·        እውን "ማኅበረ ቅዱሳን" ከመንበረ ፓትርያርክ፣ ከቅዱስ ሲኖዶስና ከጠቅላይ ቤተክህነት በላይ የሃይማኖት ጠባቂ እና ተቆርቋሪ ነውን?
·        ግርግር ለሌባ ይመቻል፤ "ማኅበረ ቅዱሳን" የዝቋላን እሳት ለማጥፋት ለአንድ ጀሪካን ውኃ 40 ብር ለሁለቱ ደግሞ 80 ብር ያስፈልገኛል ብሏል
·        በዋልድባ፣ በአሰቦትና በዝቋላ ገዳማት ጉዳይ "ማኅበረ ቅዱሳን" ዌብሳይቶችና ብሎጎች ለምን ተንጫጩ? ሌሎቹ ለምን እርጋታ ታየባቸው?
·        መንግሥት፣ ሃይማኖትና ቀጣዩ ልማታችን

"ማኅበረ ቅዱሳን" በቅርቡ ከገዳማት ሕይወት ጋር ተያይዞ በተነሳው ውዝግብ ከምንጊዜውም በላይ የፖለቲካ ኪሣራ የደረሰበት መሆኑን ልዩ ልዩ ምንጮች አረጋገጡ፡፡ ምንም እንኳን ሃይማኖታዊ ተፈጥሮ ባይኖረውም "ማኅበረ ቅዱሳን" የሃይማኖት ተቋም መስሎ በመንቀሳቀስ ብዙዎችን ቢያሳስትም፣ ዛሬ በፈጠረው የፖለቲካ ግጭት ከመንግሥትና ከሕግ ጋር ተፋጦ በመገኘቱ እውነተኛ ማንነቱ መጋለጡን የወቅቱ ሁኔታው ያስረዳል፡፡

ከአፈጣጠሩ ጀምሮ ከፖለቲካ አካሄድ ተላቆ የማያውቀው "ማቅ" ውስጥ ውስጡን ሲያተራምስ ከርሞ ዛሬ ሙሉ በሙሉ ራሱን በመግለጥ ፀረ ቤተክርስቲያንና ፀረ መንግሥት መሆኑን አሳይቷል፡፡ ይህ የሃይማኖት "ማኅበር" ነኝ ባይ ተቃዋሚ ድርጅት ቤተክርስቲያንን በእርስ በርስ ሁከት ሲያተራምስ ቆይቶ በአሁኑ ወቅት ቀይ መስመሩን አልፎ ከሕዝብና ከመንግሥት ጋር የሚያጋጨውን ድርጊት በመፈጸም ላይ ይገኛል ተብሏል፡፡


"ማኅበሩ" 40 ሺህ እስከ 80 ሺህ የሚሆኑ አባላት አሉኝ የሚል ሲሆን በመንግሥትም ሆነ በቤተክርስቲያን የአባላቱ ዝርዝር አይታወቅም፡፡ ይህ ኅቡዕ አደረጃጀቱም እጅግ አደገኛ፣ ለውንብድናም ለምለም ሁኔታን እንደሚፈጥር ልብ ይሏል፡፡ ስውር ኃይል እንደሚመራውም የማኅበሩ አመራር የሆነው ዳንኤል ክብረት እንዳጋለጠም የቅርብ ጊዜ ትዝታችን ነው፡፡ በሀገር ውስጥ እና በውጭ ሀገር የሚደረጉት የገንዘብ ዝውውሮቹ ቁጥጥር አይደረግባቸውም፡፡ ከዚህ የተነሳም አደገኛነቱን ማስተዋል ይቻላል፡፡

ቤተክርስቲያን ላወጣችው መመሪያ አይገዛም፡፡ በዚህም ምክንያት ተከታታይ መመሪያዎች ሲወጡበት ይታያል፡፡ በቤተክርስቲያን ስም የንግድ ፈቃድ ይወስዳል፡፡ ነገር ግን ለቤተክርስቲያንም ሆነ ለመንግሥት ተገቢውን ገቢ አያስገባም፡፡ ገቢዎቹንና ወጪዎቹን ቤተክርስቲያን በምታሳትማቸው ደረሰኞች እንዲመዘግብ ቢነገረውም ፈቃደኛ አልሆነም፡፡ ሀብትና ንብረቱን በነፃና ገለልተኛ ኦዲተር እንዲያስመረምር ቢታዘዝም በእምቢተኝነቱ ጸንቷል፡፡ በአጠቃላይ ሲገመገም፣ "ማኅበሩ" አደገኛነት ሊለካ የማይችል እጅግ አስጊ ነው፡፡ ጉዳዩ ፈር እንዲይዝ ከተለያዩ አካላት ለመንግሥትና ለጠቅላይ ቤተክህነት ጥቆማ ቢቀርብም በተለያዩ ምክንያቶች ችግሩ ከመባባስ በስተቀር መፍትሔ አልተበጀለትም፡፡ "ማኅበሩ" ባላሰለሰ ጥፋት ውስጥ ቀጠለበት እንጂ የመታረም ዕድል አላገኘበትም፡፡