በዲ/ን ሙሉጌታ ወልደገብርኤል
(ዲ/ን ሙሉጌታ በብዙዎች ዘንድ ከፍተኛ ተነባቢነት የነበረውና በብዙ እውነተኛ የሰነድ ማስረጃዎች የተደገፈው ማኅበረ ቅዱሳን ወይስ ማኅበረ ሠይጣን የሚለው መጽሐፍ ደራሲ ነው)
ለመግባባት ያክል የምዕራቡ ዓለም የዕድገትና የስልጣኔ ምስጢር በማውሳት ሐተታዬን ልጀምር:: ለብዙዎቻችን ግልጽ እንደሆነ የምዕራቡ አለም ፖለቲካ ከተቀረው የዓለማችን ክፍል የሕዝብ አስተዳደር የተለየና የላቀ የሚያደርገው ቢኖር የፖለቲካ መሪዎች አስተዋይነትና አርቆ አሳቢነት ለመሆኑ አያከራክርም:: ለምሳሌ ያክል "የዲሞክራሲ" ተምሳሌት የሆነችውን ሃያልዋ ሀገረ አሜሪካ የወሰድን እንደሆን በተለይ ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወዲህ በየትኛውም መስክ ያለ ተቃናቃኝ በኢኮኖሚውም ሆነ በፖለቲካው መድረክ የበላይነትዋን እንደያዘች የመዝለቅዋ ምስጢር ስልጣን ላይ የሚወጡትም ሆነ በተቃዋሚ ጎራ የተሰለፉትን የፖለቲካ መሪዎች ፖለቲካዊ አስተሳሰብ ውጤት ውጭ ሌላ ሊሆን አይችልም:: ይህ ማለት ዲሞክራትም ይሁን የሪፐብሊካን ፓርቲ አቀንቃኝ ሀገራቸው አሜሪካ በዋናነት ልትከተለው በሚገባት ፖሊሲ ላይ የጎላ ልዩነት ቢኖራቸውም የአሜሪካን ሉዓላዊነት እንዲሁም የአሜሪካ ሕዝብ ጥቅም የመጣን እንደሆነ ግን አንዱን ከሌላውን መለየት ፈጽሞ አይቻለንም:: ሀገራዊ ጥቅም በተመለከተ ዲሞክራቱም ሪፖብሊካኑም አሜሪካዊ ነው!! እናማ ከየትም አቅጣ ቢመጡ ጽሐፉን ሲያነቡ እንደ አንድ ኢትዮጵያዊ በሰከነ መንፈስና በተረጋገ ልብ እንደሚያነቡት ተስፋ አደርጋለሁ::
በያዝነው ሳምንት ከጥቂት ቀናቶች በፊት መሆኑ ነው የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር በፓርላማቸው ተገኝተው ካደረግዋቸው ንግግሮችና ከተወካዮቹም ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች መልስ ሲሰጡ ካነሱዋቸው ነጥቦች መካከል ሃይማኖትን በማስመልከት መንግስታዊ ትንታኔአቸውና አቋማቸውን ለፓርላማው ግልጽ አድርገዋል:: ጠቅላይ ሚኒስትሩ "ማህበረ ቅዱሳን" ከአልቃይዳ ጋር በማመሳሰልም ገልጸውታል:: እንግዲህ ይህን አገላለጽ/ንግግር ያዳመጠ ሰው አልቃይዳ ማለት ደግሞ ማን ነው? ምንስ ማለት ነው? ብሎ የሚጠይቅ አዋቂ ሊኖር እንደማይችል አምናለሁ::


