Click here to read in PDF
በትናንቱ ዕለት በምዕራቡ ዓለም
የሰዓት አቆጣጠር ከለሊቱ 12: 00 (pm) ይሆናል (በሀገር ቤት የሰዓት አቆጣጠር ማለዳ መሆኑ ነው) ወደ አገር ቤት ስልክ መትቼ
ነበር። የረጅም ዘመን ትውውቅና ወዳጅነት አለን ከትውውቅም ያለፈ የአባትነትና የልጅነት ያክል የጠበቀ ግኑኝነት ካለን አንድ የዕድሜ
ባለፀጋ፣ የመጻህፍት አዋቂ፣ የሲኖዶስ አባልም የሆኑት አባት (ሊቀ- ጳጳስ) በስልክ ተገናኝተን “አውግተን” ነበር። ስልክ የመደወሌ
ምክንያት ለሰላምታ ነው። መንፈስን የሚያሳርፍ መንፈሳዊ ሰላምታ ከተለዋወጥን በኋላም “ጨዋታ ጨዋታን ያመጣዋል” እንደሚባለው አገልግሎትን
በተመለከተ አንዳንድ ነገሮች ስናነሳ ያመራነው ወደ ቤተ-ክርስቲያናችን ወቅታዊ ሁኔታዎች ነበር። አንስተን ከተነጋገርንባቸው ዓበይት
ቁምነገሮች መካከል እጅግ የገረመኝና ያሳዘነኝ በመጨረሻው ዕለት በመጨረሻዋ ሰዓት በጥቂት የሲኖዶሱ አባላት ተከሰተ ሲሉ ዝቅ ባለ
ድምጽና በስብራት ያወጉኝን በጥቂቱ ለንባብ በሚያመች መልኩ ላካፍላችሁ ወደድኩ።
በዋናነት እኚህ ሊቀ ጳጳስ “ተዉ! እንዲህ ያለ ስህተት መስራቱ አስፈላጊ አይደለም። እየሆነ ያለውም
አግባብነት የለውም ደግሞም በታሪክ የሚያስጠይቅ ውርደት እየፈጸምን ነው ያለነው። … እዚህ የተሰባሰብን ብጹዓን ሊቃነ ጳጳሳት ሁላችን
ሴራው ሳይገባን ቀርቶም አይደለም ታድያ ግን ነገም በቀረን በእኛ ላይ መነሳታቸው የማይቀር ጥቂቶችን ለማሰደሰት ሲባል ስርዓተ ቤተ-ክርስቲያን
ጥሰን የገዛ ልጆቻችንን እየገፋን ነው ያለነው … ።” በማለት ድምጻቸውን ካሰሙ ጥቂቶች መካከል አንዱ ናቸው።



