Tuesday, August 28, 2012

የሲኖዶሱ የሰሞኑ ሁኔታ


Click here to read in PDF: Sinodos
  • “ሚዲያ ጥሩ እና ሌላ አቃቤ መንበር ሹሙ።” አቡነ ናትናኤል
(ዐውደ ምሕረት፤ ማክሰኞ፤ ነሐሴ 22 ቀን 2004 ዓ.ም. /awdemihret.blogspot.com// awdemihret.wordpress.com)ባለፈው ሳምንት ሐሙስ የቅዱስነታቸው የቀብር ሥነ ስርዓት ከተፈጸመ በኃላ በነጋታው ሲኖዶሱ ወደ መደበኛ ሥራው ተመልሷል። ከተመለከታቸው ጉዳዩች አንዱም የእርቁ ሁኔታ ነበር። የቅዱስነታቸው የቀብር ሥነ ሥርዓት ቀን ማታ አቡነ መልከጻዲቅ ቅዱስነታቸው ተወግዘው ነው የሞቱት ብለው መናገራቸው የእርቁን ሀሳብ አደጋ ላይ ጥሎታል።
አርብ ዕለት በነበረው ስብሰባ የእርቁ ሀሳብ ሲነሳ በርካታ ጳጳሳት የአቡነ መልከጻዲቅን ንግግር ማዘናቸውን ገልጸዋል። በተለይም የአቡነ እስጢፋኖስ አቋም ጠንካራ እና የሁሉንም ልብ ማሸነፍ የቻለ ነበር። ብጹዕነታቸው ሲናገሩ “ቀብቶ የሾመን ተወግዞ ሞተ ከተባለ እኛም የተወገዝን ነን ማለት ነው። ስለዚህ የምን እርቅ ነው የሚደረገው? እኛ የእርቅን ሀሳብ መነጋገር ከጀመርን ጀምሮ ከቅዱስነታቸው ጀምሮ ሁላችንም ስለ እነርሱ መወገዝ አንስተን አናውቅም። ምክንያቱም እርቅ የሚመጣው ያሉበትን አቋም ትቶ ነው እንጂ የወሰድኩት አቋም አይለወጥም ብሎ አይደለም። ስለዚህ ቅዱስነታቸው ሲያርፉ መነሳት የሌለበትን ርዕስ አቡነ መልከጻዲቅ ሰላነሱ በአደባባይ የተናገሩትን ንግግራቸውን በአደባባይ እስካላስተባበሉ ድረስ የእርቅ ሀሳብ አይኖርም” በማለት በአጽንኦት ተናግረዋል። ይህንንም ሀሳብ አብዛኛዎቹ ጳጳሳት ተቀብለውታል።

ከዚህም ጋር ተያይዞ አቡነ ሳሙኤል አቡነ ሉቃስ እና አቡነ ህዝቅኤል “የስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ስለሆንን የአዲስ አበባ አድባራትን አስተዳዳሪዎችን እና የጠቅላይ ቤተክህነት ሰራተኞችን ሰብሰብን ማናገር አለብን።” በማለታቸው በብዙሀኑ ዘንድ ተቃውሞ ገጥሟቸዋል። “የጠቅላይ ቤተክህነቱን ሰራተኞች ማነጋገር ጠቅላይ ስራ አስኪያጁ ስራ ነው የአዲስ አበባ አድባራትን እና ገዳማትን ስራ አስኪያጆች ማናገር የሀገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስ ሥራ ነው። ያለስራችሁ አትግቡ።” ተብለዋል።  የቀድሞውንም ቢሆን ይህ ጊዜያዊ ኮሚቴ የተቋቋመበት አላማ የአቃቤ መንበሩ እና የጠቅላይ ሥራ አስኪያጁን ስራ ተረክቦ ሁሉቱንም ከጨዋታው ውጭ የማድረግ አላማ ይዞ ስለነበር አላማውን ለማስፈጸም አንድ እርምጃ ያደርሰኛል ይወስደኛል ብሎ ያሳበውን ሀሳብ ቢያቀርብም የኮሚቴው አባል የሆኑት አቡነ እስጢፋኖስ ጉዳዩን መቃወማቸው እነ አባ ሳሙኤልን አስደንግጧቸዋል። ይህ አካሄድ ከተሳከ በመዋቅሩ በኩል ያለውን የስራ አስኪያጁን እና የአቃቤ መንበሩን ግንኙነት ሙሉ በሙሉ በማጥፋት ሁሉቱንም ሥራ አና ግንኙነት አልባ አድርጎ ያስቀምጥ እንደነበር ታዛቢዎች ተናግረዋል። ሁለቱ ደግሞ ተገናኝተው የማይሰሩ ከሆነ ስራው በግል ኮሚቴዎች በትክክል ሊሄድ እንደማይችል የታወቀ ነው። ይህ ኮሚቴ በማኅበረ ቅዱሳን በኩል ሲቋቋምም የነበረው አላማ ቅዱስነታቸው በህይወት እያሉ አይነኩብን ሲሉዋቸው የነበሩትን ህጎች ለእነሱ በሚመቻቸው መልኩ አስተካክለው ከጨረሱ በኃላ የፓትርያርክ ምርጫ ለማድረግ ነው።
ከዛ ደግሞ እነዚሁ ጳጳሳት ስራ አስፈጻሚው ህግ ይውጣለት ብለው ሲጠይቁ አሁንም አቡነ እስጢፋኖስ “የምን ህግ ነው የሚወጣለት? ሲኖዶሱ የራሱ ሕግ አለው። ይሔ ድጋፍ ሰጪ ኮሚቴ አስከሆነ ድረስ ከፈለገ ከቋሚ ሲኖዶሱ ጋር ይሰብሰብ እንጂ ሌላ ህግ አይወጣለትም።” ሲሉ ተቃውመዋል። ይህንን ሀሳብ አብዛኛዎቹ ሊቃነ ጳጳሳት ደግፈዋል።
የስብሰባው አካሄድ ግራ የጋባቸው እና የጭቅጭቁ መብዛት ያስመረራቸው አቡነ ናትናኤል እኔ ሽማግሌ ነኝ በስተርጅና መዋረድ አልፈልግም ይዘታችሁ ደስ አላለኝም ሲኖዶሱን የሚመራው መንፈስ ቅዱስ ነው እስካልን ለምን አንረጋጋም? በዚህ እድሜዮ ውርደት ከመቀበልና ሽምግልናዬን ከማበላሸት  ሚዲያ ጥሩና ሌላ ሹሙ እኔ ግን ስራውን እለቃለሁ። በማለት ተነስተው ሊወጡ ሲሉ  በእድሜ ገፋ ያሉት ጳጳሳት ሀሳቡን በመቃወማቸው እና በተለይም አቡነ ፊሊጶስ “አባታችን እንዲህ አይሁኑ እየተረዳዳን እንሰራለን በሆነ ባልሆነው ነገር እየተደናገጥን ቤተክርስቲያንን አሳልፈን መስጠት የለብንም” በማለታቸው እንደገና ተመልሰው ተቀምጠዋል። እነ አባ ሳሙኤልም ከአቡነ ናትናኤል የእለቃለሁ ንግግር በኋላ ረገብ ብለዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለም ከጠቅላይ ሚኒስቴሩ ዕረፍት ጋር ተያይዞ የፓትሪያርክ ምርጫው ላይ ማኅበረ ቅዱሳን የያዘውን አቋም መቀየሩ ታውቋል። ጠቅላይ ሚኒስቴሩ በሕይወት እያሉ መንግስት ጣልቃ ሊገባ ስለሚችል አቡነ ሉቃስን ብናደርጋቸው ይሻላል የሚል አቋም የነበራቸው ሲሆን አሁን ጠቅላይ ሚኒስቴሩ ካረፉ ባለስልጣናቱ ጊዜያቸውን በውስጥ ሽኩቻ ማጥፋታቸው አይቀርም በሚል በአንደኝነት ይዘዋቸው የነበሩትን አቡነ ሉቃስን ወደ ሶስተኛ ቦታ አውርደው አንደኛ እጩ አድርገው አቡነ ያሬድን ሲይዙ በሁለተኛነት ደግሞ አቡነ ማቴዎስን አስቀምጠዋል።
        ሲኖዶሱን መንፈስ ቅዱስ ይመራዋል ተብሎ ቢታመንም በአሁኑ ሰዓት ሲኖዶሱን እያመሱት ያሉት ማኅበረ ቅዱሳንን እና ዋነኛ ወኪላቸው ማንያዘዋል መሆናቸው ይታወቃል። ማንያዘዋል በቤተክህነት አካባቢ ይሔ ነው የሚባል ስራ ሳይኖረው ውሎውም አዳሩም እዛው ሆኗል። በሁሉም ነገር ውስጥ እየገባ ለማቡካት ይሯሯጣል። አባቶችን በተለያየ የሀሳብ ውዥንብር ውስጥ እየከተተ ግራ ያገባል። ይሁንና ለማኅበረ ቅዱሳንም ቢሆን ጳጳሳቱን በራሱ የሀሳብ አሰላለፍ ማስኬድ አቡነ ጳውሎስን ለመቃመም እንደማስተባበር የቀለለ ሆኖ እንዳላገኘው የሰሞኑ ሁኔታ ያስረዳል።

1 comment:

  1. Thank you for your update info. የእግዚአብሔርን ድንቅ ሥራ ዝም ብሎ ማየቱ ይሻላል። ማቅ እንቅልፍ ብያጣም እግዚአብሄር ሁሉን ቻይ ስለሆነ ድንቅ ሥራውን ዛሬም እያየን ስለሆነ ማቅ ጠንቀቅ ብሎ ይሻላቸዋል.

    ReplyDelete