Saturday, May 12, 2012

ደብዳቤው የማን ነው?

click here to read in PDF
·        በጠቅላይ ቤተ ክህነት ሰራተኞች ስም “ተበተነ” የተባለው ደብዳቤ የተረቀቀውና የተሠራጨው በማኅበረ ቅዱሳን መሆኑ እና የጠቅላይ ቤተክህነት ሠራተኞች ሐሳብ አለመሆኑ ተገለጸ
                        ምንጭ፦ አባ ሰላማ
በዓመት ሁለት ጊዜ የሚደረገውን መደበኛ የሲኖዶስ ስበስባ ከመበጥበጥ ቦዝኖ የማያውቀውና የተለያዩ የራሱን አጀንዳዎች የቤተክርስቲያኗ አጀንዳዎች አስመስሎ በመቅረጽና በተለያዩ መንገዶች አሳስቶና አስፈራርቶ የሀሳቡ አስፈጻሚዎች ባደረጋቸው አንዳንድ ጳጳሳት በኩል ለሲኖዶስ እንዲቀርብለት ከፍተኛ ገንዘብ እየመደበ ሲያውክ መኖሩ የሚታወቅ ነው። በዚህ በግንቦቱ ሲኖዶስ ላይም ቤተክርስቲያኗን የሚበጠብጥበትን መላ ሲዘይድ እንደሰነበተና በጠቅላይ ቤተ ክህነት ሰራተኞች ስም ደብዳቤ አርቅቆ እንደበተነ ውስጥ አዋቂ ምንጮች እየተናገሩ ነው።የጠ/ቤተ ክህነቱ ሠራተኞችየዳኛ ያለህ! ለቤተ ክርስቲያኒቱ ዳኝነት ይታይላትየሚል ጽሑፍ ለቅዱስ ሲኖዶስ አባላት አሰራጩ” በሚል ርእስም፣ በግልጽ የሚሰሩት የማኅበሩ “ስውር” ድረገጾች ደጀሰላምና አንድ አድርገን ወሬውን አናፍሰውታል።
ማኅበረ ቅዱሳን በግልጽም በስውርም የሚንቀሳቀስ ማኅበር ነው። ማኅበሩ ግልጽም ስውርም አመራሮች አሉት። ማኅበሩ ግልጽም ስውርም አካሄድ አለው። የማኅበሩን እንቅስቃሴ በግልጽም በስውርም የሚያንጸባርቁ ድረገጾች አሉት። ማኅበሩ በስሙ በግልጽ የሚያቀርባቸው፣ ስሙን ሳይጠቅስ በስውር በሌሎች ስም የሚበትናቸውና የሚጠይቃቸው የጽሑፍ ጥያቄዎችም አሉት። ባለፈው ጥቅምት ለሲኖዶስ አባላት በስሙ ያስገባውን፣ እንዲሁም በአዲስ አበባ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ስም “አገር ሁሉ ይወገዝልኝ” ሲል በሌሎች ስም ያስገባቸውን ማመልከቻዎች ማስታወስ ብቻ ይበቃል። ከሰሞኑ የጠቅላይ ቤተክህነት ሰራተኞች በተኑት ያለው ደብዳቤም አዲስ ነገር ይዞ አልመጣም። በውስጡ ማኅበሩ በአሁኑ የቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባ በአጀንዳነት እንዲያዙለት የሚፈልጋቸውና ከጎኔ ይቆማሉ ብሎ ለሚያስባቸው ጳጳሳት ያስጨበጣቸው አጀንዳዎቹ ናቸው። ይህንንም ለእርሱ “ስውር” ለታዛቢ ግን ግልጽ በሆኑት ድረገጾቹ ቀደም ብሎ ሲነዛው ነው የከረመው። 
ደብዳቤው ውስጥ የተነሱ ጥያቄዎችን ምናልባት በተለያየ ምክንያት የስራ ዝውውር የተደረገላቸውና በጡረታ ተገለሉ የተባሉ ከማቅ ጋር ንክኪ ያላቸው ሰዎች አንስተውት ሊሆን ይችላል የሚል ግምት እንኳን ቢኖር፣ የእነርሱ ጥያቄ ሌላ መልክ ሊይዝ የሚችልበት አሳማኝ ምክንያት አይኖርም። የግለሰቦቹ ጥያቄ መሆን ያለበት፣ ከስራዬ ለምን ተባረርሁ? ወደስራዬ መልሱኝ? ለምን ከዚህኛው ክፍል ወደዚያኛው ክፍል አዛወራችሁኝ? ሰርቼ ሳልጠግብ ለምን በጡረታ አገለላችሁኝ? ወዘተ እንጂ “የሰራተኞቹ” በተባለው ደብዳቤ እንደተገለጸው ሊሆን የሚችልበት አንድም ምክንያት የለም። 

ሰራተኞቹም በአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ላይ ለክፉ ቀን እንጠቀምበታለን በሚል መረጃ ሲሰበስቡ ኖረዋል የሚለው ብዙ ኣስኬድም። በሃይማኖት ሽፋን በመንቀሳቀስ የራሱን አጀንዳ ጥቂት የስራ ዝውውርና ሌላም አስተዳደራዊ እርምጃ የተወሰደባቸው ሰራተኞች ጥያቄ አስመስሎ ደብዳቤው ያዘለውን ድብቅ ሃይማኖት ለበስ ፖለቲካዊ አቋም ያቀረበው ራሱ ማቅ እንጂ በስማቸው የተነገደባቸው የጠቅላይ ቤተክህነት ሰራተኞች አይደሉም። እንዲህ ያለው ተግባር ድብቅ አጀንዳዎቹን በሃይማኖት ሽፋን ሲያቀርብ የኖረውና ይህን ጠባዩን መለወጥ ያልቻለው የማኅበረ ቅዱሳን እንጂ የሌላ የማንም ሊሆን አይችልም።

በቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ላይ ያተኮረውና በተለይም ቅዱስ ፓትርያርኩ እና አቡነ ገሪማ ላይ ያነጣጠረው ሚያዝያ 27 ቀን 2004 .ተጻፍኩኝ የሚለው ደብዳቤ የያዛቸው ሀሳቦች የማኅበሩ ሀሳቦች መሆናቸውን ዋና ያልናቸውን ነጥቦች በመንቀስ ከዚህ እንደሚከተለው ለመሄስ እንሞክራለን።

ደብዳቤው ዓለም ግን ቤተ ክርስቲያኒቱ የት እንዳለች ከነችግሯ ያውቃታል፤ እናንተንም ያውቃችኋል፤ በበኩላችንም እንዴት እንደምታውቁት ከአሁን በፊት የገለጽንላችኹ ቢኾንም እንደገና ብናስታውሳችኹ አይከፋም፡፡” ይላል። በዚህ ውስጥ “ከአሁን በፊት የገለጽንላችሁ” የሚል ሐረግ እናገኛለን። በስማቸው የተነገደባቸው የቤተክህነት ሰራተኞች ከዚህ ቀደም ምን ብለው ነው? መቼ እና በምን ምክንያ? የሚሉትን የአሉባልታ መንደር የሆኑት ድረገጾቹም ሆኑ በማኅበሩ ተረቅቆ የተበተነው ደብዳቤ ምንም ያለው ነገር የለም። ምናልባት ግን ማኅበሩ ከዚህ ቀደም አንዳንድ ጳጳሳትን በግል “ነውራችሁን የሚገልጽ መረጃ በእጄ ይገኛልና የምላችሁን አድርጉ፤ አሊያ ዋ!” እያለ ያስፈራራበትን አጋጣሚ ይሆናል የጠቀሰው የሚል ግምት አለን። ለማስታወስ የፈለገውና በመጀመሪያው ተራ ቁጥር ላይ የተቀመጠው ሀሳብም ይህንኑ ያመለክታል።

“ከመካከላችኹ የሚያሳፍርና አንገት የሚያስደፋ ተግባር ስለአለባቸው በልበ ሙሉነት አፋቸውን ከፍተው ስለ ቤተ ክርስቲያናቸው ጉዳይ መናገር የማይችሉ የተወሰኑ ጳጳሳት መኖራቸው በትክክል ይታወቃል፡፡ እነዚህ ሰዎች ቤተ ክርስቲያን ስትቃጠል ቢያዩና የሚያቃጥሉትም አቡነ ጳውሎስ ከኾኑ መልካም ነው እያሉ ከሚያጨበጭቡ በስተቀር መከላከል አይፈልጉም፤ ስማቸውም እግዚአብሔር በፈቀደ ጊዜ ይጠቀሳል፤ ከነተግባራቸውም ይተረኩ ይኾናል፡፡” ማኅበሩ አንዳንድ ጳጳሳትን በተለያዩ ነውሮች አግኝቻቸዋለሁ እያለና ይዤባቸዋለሁ የሚለውን የፎቶ ወይም ሌላ ማስረጃ እየጠቀሰ የሚላቸውን እንዲያስፈጽሙለት የፍላጎቱ ተገዢ ያደረጋቸው ጳጳሳት መኖራቸውን ከዚህ ቀደም ስንጠቅስና እንደአስፈላጊነቱ በአንዳንዶቹ ላይ መረጃውን በተወሰነ መልኩ ይፋ ስናደርግ መቆየታችን ያታወሳል። ምናልባት ማኅበሩ ሲያስፈራራበት ከሚኖር ይፋ መደረጉ አንዳንዶቹን ጳጳሳት ከማኅበረ ቅዱሳን ማስፈራራትና ተገዢነት ነጻ ሊያወጣቸው ይችላል የሚል እምነት ስለነበረን ነው የተወሰኑትን አባቶች አንዳንድ አሳፋሪ ተግባር ይፋ ማድረግ የጀምርነው። መደበቁ ማቅ እያስፈራራበት ተገዢው ከማድረግ ያለፈ ፋይዳ ስለሌለው፣ ጳጳሳቱ ከዛሬ ነገ ነጻነታቸውን ያውጃሉ ብለን ነው መግለጣችን። ነገር ግን እነርሱም ከፍርሀትና ለማቅ ከመገዛት ነጻ ሊወጡ አልቻሉም። ማቅም አሁን “በእጄ ብዙ ገመና ገላጭ መረጃ አለኝ” እያለ አይኑን በጨው ታጥቦ ማስፈራሪያውን በዚህ ደብዳቤ ውስጥ እንደገና አንስቷል። ቀድሞ በየሰዉ ጆሮ ሹክ ሲለው የነበረውን፣ አገር ያወቀውንና ፀሀይ የሞቀውን እውነት እንዲህ በአደባባይ መናገሩ ካልሆነ በስተቀር ነገሩ አዲስ አይደለም። ምናልባት በእርሱ “ስውር” ድረገጾች ከወጣ በሌሎች ከተነገረው ይበልጥ ጳጳሳቱ ትኩረት ይሰጣሉ ብሎ አስቦ ከሆነ ተሳስቷል። ምናልባትም ከማኅበሩ ጋር እንዳይቆራረጡ ያሰጋል። ምክንያቱም የበሰበሰ ዝናብ አይፈራምና።

እናንት ለማቅ ያደራችሁ ጳጳሳት ሆይ! መረጃዎቹ በደጉ ጊዜ ለክፉ ቀን ይሆነኛል ብሎ “ከመረጃችሁ” ከማቅ መንደር የተገኙ መሆኑን ብታውቁ ምን ይሰማችሁ ይሆን? እርሱም እኮ በደብዳቤው ይህን እንዳረጋገጠ ማመን አለባችሁ። ከዚህ የወዳጅ ጠላት ማህበር አገዛዝ ነጻ የምትወጡት መቼ ነው?

ሂሳችንን እንቀጥል
“መብላታቸውንና መተኛታቸውን እንጅ በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ ችግር ይኑር አይኑር በአጠቃላይ በአሁኑ ጊዜ ቤተ ክርስቲያኒቱ የት እንዳለች የማያውቁ የዋሃን አባቶች እንዳሉ የሚካድ ነገር አይኾንም፡፡ እነዚህ የዋሃኑ አባቶች ስለ ቤተ ክርስቲያን ጉዳይ የጦፈ ክርክር ቢነሣ የክርክሩን ሂደት አለማወቃቸው ብቻ ሳይኾን አጀንዳው ምን እንደ ኾነ የመገንዘብ አቅም የሌላቸው ናቸው፡፡ የሚያውቁት ነገር ቢኖር አባ ገሪማ እጃቸውን ሲያወጡና ሲያወርዱ እየተከታተሉ እጅ ማውጣትና ማውረድ ብቻ ነው፤ ማለትም የአባ ገሪማ እጅ መውጣት መውረዱን አጥብቀው ከመከታተል በቀር ከዘገምተኞች የሚሻሉበትን መመዘኛ በጭራሽ አላገኘንላቸውም፡፡ በመኾኑም የተደላደለ አእምሮ ያላቸው ሰዎች ሊቀመጡበት የሚገባው ወንበር ላይ እነዚህ ደመ ነፍሶች ተቀመጡበትና ቤተ ክርስቲያናችን ተጎዳች፡፡” ይላል ደብዳቤው።

በዚህ ነጥብ ስር ማኅበረ ቅዱሳን “የዋሃን” በሚል ቅጽል የጠራቸው አባቶች አሉ። እነዚህ አባቶች በአባ ገሪማ የሚመሩና ከመብላትና ከመተኛት በቀር (በሌላ አነጋገር “በላ-ተኛ” ናቸው ማለት ነው) ምንም የማያውቁ፣ “ዘገምተኞች” እና “ደመ ነፍሶች” መሆናቸውን ጠቅሶ ቤተክርስቲያን በእነርሱ ምክንያት እንደተጎዳች አትቷል። ይህ ደብዳቤ የማኅበረ ቅዱሳን ነው ለማለት ያስደፈረንን ሌላ ነጥብ እዚህ ውስጥ አግኝተናል። ማኅበሩ ብዙዎቹ ጳጳሳቱ ተመሪዎች እንጂ የራሳቸው አቋም እንደሌላቸው እየነገረን ነው። እዚህ ላይ ያበሳጨው ታዲያ ማቅ እንዳሻኝ እንዳልነዳኋቸው አሁን ፊታቸውን አዙረውብኝ በአቡነ ገሪማ ለምን ይመራሉ? ነው። ባለፈው እንዳደረግኩት ለምን በእኔ አይመሩም?  በየጊዜው ረብጣ ብር መመደብ አልችልም፤ አንዳንዴም የከዚህ በፊቱን አስባችሁ በነጻ ለምን አትደግፉኝም? የሚል ነው ጠቡ።

ቀጣዩ ነጥብ ደግሞ እንዲህ ይላል፤
“በልዩ ልዩ ጥቅም የተያዙ አባቶችም አሉ፡፡ እነዚህም ለራሳቸው እና ለቤተሰባቸው ቢዝነስ መሥራት እንጅ ስለ ቤተ ክርስቲያን ጉዳይ ቢያውቁም ምናቸውም አይደለም፡፡ በተለይም የተጠቃሚዎች መሪና አርኣያ የኾኑት አባ ገሪማ እንደ ማንኛውም ጳጳስ ሀገረ ስብከታቸው ላይ የማይገኙ ከመኾናቸውም በላይ መንበረ ፓትርያርክ ውስጥ ቁጭ ብለው በነጻ እንጀራ ይበላሉ፡፡ ጮማውና ውስኪው ሳይቀር ከአቡነ ጳውሎስ ጋራ መንበሻበሽና ሽርሽር ሲያስፈልግም በቤተ ክርስቲያናችን ገንዘብ በሀገር ውስጥም ኾነ በውጭ ሀገር እንደ ፈለጉ መዝናናትና መንከራተት ነው፡፡ ብቻ እነዚህ ሰዎች ምን ጉድ እንዳላቸው አይታወቅም እንጅ በጭራሽ ተለያይተው ማደር አይፈልጉም፡፡ የቤተ ክርስቲያንን ሀብት አታባክኑ፤ የአግዚአብሔርን ሕግ አትጣሱ ብሎ የሚቆጣ ሽማግሌም ጠፋ፤ ምን ይሻላል? በእውነቱ እነዚህ በልብስና በስም አባቶችን የሚመስሉ ሁለቱ ሰዎች ነውረኛና ክፉ በኾነ ፍቅር ተጠምደው ቤተ ክርስቲያኒቱን አጠፉ፡፡ በዚህ ክፉ ፍቅር የተነሣም አባ ጳውሎስ ሰው እንዲገደል መመሪያ ቢሰጡ አባ ገሪማ ሰውን ከመግደል ወደ ኋላ እንደማይሉ ሰው ሁሉ ሊያውቃቸውና ሊጠነቀቅባቸው ይገባል፡፡ እኛ ግን የቤተ ክርስቲያን አምላክ ይፍረድ፤ ታሪክም ይውቀስ፤ በሕዝብ ዘንድም መጋለጥ ይምጣ ከማለት በቀር ለጊዜው ዝም ብለናል፡፡”

ለመሆኑ ጳጳሳትን በጥቅማጥቅም በመግዛትና በመያዝ ማኅበረ ቅዱሳንን የሚያህል አለ ወይ? በጥቅምት 2004 የሲኖዶስ ስብሰባ በነፍስ ወከፍ 200 ሺህ ብር መድቦ ሲኖዶሱን በገንዘብ ለመንዳት የተቻለውን ሲያደርግ አልነበረም? ይህንንም ከማንም በላይ ስለሚያውቅና እርሱም በደካማ ጎናቸው በጥቅም ይዞ ያሻውን ለማስደረግ ሲጥር ነው የኖረው። ዛሬ ምን ተገኘና ነው ምስጢሩን የሚያወጣው? እንደጥቅምቱ የሚያቀርበውን የብር አምሃ ስላልመደበና ያስለመዳቸው ጥቅም ስለቀረ ገሸሽ አድርገውት ነው ወይስ ርእሱን አንስቶ በዚህ አጋጣሚ አቡነ ገሪማን ሊነካ ፈልጎ ይሆን? መቼም በዚህ ደብዳቤ ማኅበረ ቅዱሳን በዋናነት ማጥቃት የፈለገው ፓትርያርኩንና አቡነ ገሪማን ነው። በተለይ አቡነ ገሪማን እንዲህ ለምን ጠመዳቸው ቢባል? የዛሬን አያድርገውና በጥቅም ተገዝተው ለጥቂት ወራት የማኅበሩን ፈቃድ ሲፈጽሙ ለቆዩት ለአባ ኅሩይ ትእዛዝ ማስተላለፋቸውና አባ ኅሩይም እንቢ በማለታቸው ከቦታቸው ለመነሳታቸው ምክንያቱ አባ ገሪማ ናቸው ብሎ ስላሰበ እንደሆነ ግልጽ ነው። ለዚህ ነው ስማቸውን የአረፍተ ነገሮቹ ማጣፈጫ አድርጎ በተደጋጋሚ የጠቃቀሳቸው።

ደብዳቤው ከአቡነ ገሪማ በላይ ትልቅ ውርጅብኝ ያወረደው በፓትርያርኩ ላይ ነው። በስማቸው በተነገደባቸው ጠቅላይ ቤተክህነት ሰራተኞች ላይ ደረሰ የተባለው አስተዳደራዊ በደል ነው። ይህን የሚያሳይና በደል አድራሾች በተባሉት ላይ የህሊና ፍርድ እንኳን እንድንሰጥ የሚያደርግ አንድም ተጨባጭ ነገር ግን አልቀረበም። ከዚያ ይልቅ ከዚህ ቀደም በሌላ ጉዳይ አቡነ ጳውሎስ አደረጉት እያሉ በመንደር ብሎጎቻቸው ሲያወሩና ሲያስወሩ የነበረውን ነገር ነው እዚህ ላይ የደገሙት። ስለዚህ ክሱ ሁሉ ፍየል ወዲህ ቅዝምዝም ወዲያ ሆኗል። እስኪ አንባቢ የህሊና ፍርድ ይስጥ፤ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ሰራተኞችን ጉዳይ ከአቡነ አብርሃም መሻርና ከአሜሪካ መነሳት ጋር ምን አገናኘው? የሚከተለው ነጥብ እርሱን የተመለከተ ነው። 

“ጳጳሳትን መሾም፣ መሻርና ማገድ የቅዱስ ሲኖዶስ ሥልጣን እንደ ኾነ በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ 19/4 22(1-3) እና 23 የተደነገገው ሲታይ የሁሉንም ጳጳሳት መብት የሚመለከት ነው የሚመስለው፡፡ አቡነ ጳውሎስ ግን ሊያጠቋቸውና ሊበቀሏቸው የፈለጓቸውን ሊቀ ጳጳስ በየጊዜው ሲያግዷቸውና ሞራላቸውን እየነኩ ግፍ ሲፈጽሙባቸው አባቶች እያያችኹና እየሰማችኹ ዝምታ መምረጣችኹ አጠያያቂ እየኾነ ነው፡፡ ምናልባት እርስ በርሳችኹ እንዴት ነው? እናንተም ትመቀኛኛላችኹ እንዴ?” በዚህ ውስጥ የተነገረው የማቅ ቀንደኛ ደጋፊ ስለሆኑት አባ አብርሃም ነው። ታዲያ የእርሳቸው ከአሜሪካ መነሳትም ሆነ የአቡነ ፋኑኤል ወደ አሜሪካ መላክ ለጠቅላይ ቤተክህነት ሰራተኞች ምናቸው ነው? ባይሆን ለማቅ ትልቅ የራስ ምታትና ብዙ ሕልሙን ያከሸፈ ዱብ ዕዳ እንደሆነ እናውቃለን። ለዚያ ነው የእነርሱን ትልቅ ጥያቄ የጠቅላይ ቤተክህነት ሰራተኞች ጥያቄ አስመስሎ ያቀረበው። መቼም የማቅ ስውር አመራሮች በግልጽ አመራሮቹ መጠየቅ የፈሩትን ጥያቄ በጠቅላይ ቤተክህነት ሰራተኞች ስም መጠየቃቸው የማይታበል ሀቅ ነው። ጠቅላይ ቤተክህነትም ይህን ስለሚገነዘብ ሰራተኞቹን ለአውጫጪኝ አይጠራም እንጂ ማቅ እኮ ሰራተኞቹን ጉድ ሰርቷቸዋል ማለት ይቻላል።
   
ሌላውን ዝባዝንኬ እንተውና ደብዳቤው እጅግ በድለውናል ያላቸውን አቡነ ጳውሎስን ወደከሰሰበት ዋና ነጥብ እንለፍ። በሰራተኞቹ ላይ ደረሰ የተባለው በደል አስተዳደራዊ ሊባል የሚችል በደል ነው። ክሱም ከዚህ አንጻር መቅረቡ ተገቢነት አለው። ደብዳቤው ግን አቡነ ጳውሎስን የሃይማኖት ሕጸጽ አለባቸው በሚል እየከሰሳቸው ነው። ምክንያቱም በዚህ ካልሆነ በቀር ቅዱስነታቸውን አስወግዳለሁ ብሎ የሚንቀሳቀስበት አማራጭ የለውም። ደብዳቤው ያቀረበው ሃይማኖታዊ ክስ ጥንተ አብሶን ደግፈው ጽፈዋል የሚል ነው። የጥንተ አብሶ ጉዳይ በሚገባ መታየት ያለበትና ቅዱስ ሲኖዶስ አጢኖ ውሳኔ ሊሰጥበት የሚገባ እንደሆነ ይሰማናል። ይሁን እንጂ ጥንተ አብሶ የነገረ ሃይማኖት ክፍል ባለመሆኑ ያን ያህል ሊያነጋግር ባልተገባ ነበር። ለወገበነጩ ማቅ ግን እንኳን ጥንተ አብሶ የመብል ጉዳይም ሃይማኖት ነው። ታዲያ ሰራተኞቹ ላይ ደረሰ የተባለው በደልና ጥንተ አብሶ ምን አገናኛቸው?

ማቅ ጥያቄውን ሁሉ ሃይማኖት ማልበስ ስለሚፈልግ በሌላ ጉዳይ የተጣላውን ወይም ያላስደሰተውን ሁሉ በዚህ ነገር በድሎኛል ከሚል ይልቅ መናፍቅ ነው ተሀድሶ ነው ማለት ይቀናዋል። አቡነ ጳውሎስ በቤተክርስቲያናችን መሪነታቸው የወሰዷቸው አንዳንድ እርምጃዎች ማቅን ስላላስደሰቱት አላስደሰቱኝም፤ እኔን የሚጎዳ ውሳኔ አሳልፈዋል ማለት ሲገባው፣ እርሱ ግን የምእመናንን ስሜት ለመቀስቀስና እድሜውን ለማራዘም ስለምንፍቅናና ስለተሀድሶ ያወራል። ስለዚህ ነው ደብዳቤው በማቅ የተረቀቀና በሰራተኞቹ ስም የተበተነ የማቅ ሀሳብና ተግባር ነው የምንለው።

በመጨረሻ ደብዳቤው የጠቀሰው በልማት ኮሚሽን ውስጥ ተደረገ ስላለው አሿሿም ነው።
የልማት ኮሚሽን ኮሚሽነርና የቦርድ አባላቱ የሚመረጡት በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ እንደ ኾነ በሕገ ቤተ ክርስቲያኗ አንቀጽ 7(15)() እና () መደንገጉ እየታወቀ / አግደው በግል ወዳጅነት ያለስጦታቸው ገብተው ኮሚሽኑን እየገደሉት ናቸው፡፡ ከቦርዱ አባላት መካከል በተለይ እነ (/) ቆስጠንጢኖስ የሚባሉት ለዘመናት ተተክለው የቤተ ክርስቲያኒቱን ኮሚሽን እየመጠመጡት ነው፡፡ አሁንም ይህ ከጠቅላይ ቤተክህነት ሰራተኞች ጉዳይ ጋር ምን እንዳገናኘው ግልጽ አይደለም። ከዚህ ይልቅ ነውራቸው ከማኅበሩ እጅ አይወጣም ተብለውና በጓዳ ለፓትርያርክነት ታጭተው ባለበት ሁኔታ፣ ውስጥ አዋቂያቸው በነበረው በዘሪሁን ሙላቱ ብእር “የጳጳሱ ቅሌት” ተብሎ ምስጢራቸው ድንገት አደባባይ ከወጣ በኋላ፣ ማኅበሩ ፊት ሳይነሳቸው “ወዳጅነቱን” እያሳየ አብሯቸው እስካሁን ለዘለቀው ለአባ ሳሙኤል ተቆርቁሮ መሆን አለበት፤ ልማት ኮሚሽን የአባ ሳሙኤል ቢሮ ስለሆነ ከዚያ ጋር ለማያያዝ ይሆናል ይህ ነጥብ የተነሳው እንጂ፣ የጠቅላይ ቤተክህነት ሰራተኞችን የሚመለከት ሆኖ አይደለም።

ሲጠቃለል
ደብዳቤው ፣ አንድ አድርገን ቀደም ብሎ ቅዱስ ሲኖዶስ ይወያይባቸዋል ሲል ከማኅበሩ ስውር አካሄድ ክፍል ደርሶት ግንቦት 1/2004 ያስነበበን ጽሁፍ ግልባጭ ነው።
·        “ማኅበረቅዱሳን የመምህር ዕንቁባህርይ ተከሰተ የሰንበት /ቤቶች ማደራጃ መምሪ ዋና ሃላፊነት ሹመት ህገወጥ መሆኑን አስታወቀ፡፡” (ይህ ለአባ ኅሩይ መነሳትና ለመምህር ዕንቆ ባሕርይ መሾም ምክንያት ናቸው በሚል በአቡነ ገሪማ ላይ ከወረደው ውርጅብኝ ጋር ይገናዘባል)
·        “የአቡነ ጳውሎስና የአቡነ ሣሙኤል ውዝግብ የአሁኑ ቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባ ዋነኛ አጀንዳ እንደሚሆነ እየተነገረ ነው፡፡” (ይህ መጨረሻ ላይ ከተጠቀሰው ከልማት ኮሚሽኑ ጉዳይ ጋር ተያያዥነው አለው)
·        “ጥንተ አብሶንና የተሃደሶ መናፍቃን አስተባባሪዎችን አስመልክቶ ቅዱስ ሲኖድስ ሃይማኖታዊ ውሳኔ ይሰጣል ተብሎ ይጠበቃል፡፡” (ይህ ደግሞ አቡነ ጳውሎስ ከስልጣናቸው እንዲነሱ እየቀሰቀሰ ካለው ጉዳይ ጋር የተገናኘ ነው)
·         “የገዳማትንና የሰሜን አሜሪካን አስመልክቶ በስፋት እንደሚነጋገር ይጠበቃል፡፡” (ይህም፣ በተለይ የሰሜን አሜሪካው ጉዳይ ከአቡነ አብርሃም  መነሳት፣ በዚያ ከተከፈተው ቢሮ ጋር በተያያዘ ሲኖዶሱ ይወያያል ካሉት ጋር ይያያዛል)

ታዲያ ደብዳቤው የማነው? የጠቅላይ ቤተክህነት ሰራተኞች ወይስ የማኅበረ ቅዱሳን?
ከ http://www.abaselama.org የተወሰደ

No comments:

Post a Comment